የቱሉ ፎርሳ ደራሲ ማነው?


እነሆ ቱሉ ፎርሳ ከተጻፈ በያዝነው ነሐሴ ወር ድፍን 50 ዓመት ሞላው። ጸሐፊውን የበላ ጅብ ግን እስካሁን አልጮኸም። ይሄ አይገርምም ወይ ታድያ? ስለ ስራው ውበት፣ ቅለት፣ ዘመን ተሻጋሪነት እጅግ ሌላም ሌላም ሌላም ነገር የማውራት ሀሳቡ የለኝም። በሀገራችን ሥነ ጽሑፍ ታሪክ ግን እንደ ቱሉ ፎርሳ የራሱ ቀን ኖሮት የሚዘከር ሌላ ስራ ያለ አይመስለኝም። ምስጋና ለላብ አደሮችም ቀን ይሁንና። እና በዚሁ ሁሉ ዓመታት ውስጥ ጸሐፊው አለመታወቁ አይገርምም ወይ ታድያ? 


ለመጀመሪያ ጊዜ ቱሉ ፎርሳን ያነበብኩት "ጭጋግና ጠል" መጽሐፍ ላይ በ2002 ዓ.ም. ነው። ጭጋግና ጠል የያዘውን የጸሐፊያንን ስብስብ አስቡት። ጭጋግና ጠል - በሥነ ጽሑፍ ታሪካችን፣ ትልልቅ አሻራዎችን ያሳረፉ ወጣት እና አንጋፋ ጸሐፊያንን ስራ ያካተተ መጽሐፍ ነው። ዳኛቸው ወርቁ፣ በአሉ ግርማ፣ ስብሃት ገብረእግዚአብሔር፣ ባሴ ሃብቴ፣ አዳም ረታ፣ ደምሴ ፅጌ፣ ሰርቅ ዳንኤል፣ መሐመድ አሊ፣ ሰለሞን አያሌው እና ፍሬህይወት ተሰማ ሥራዎቻቸው የተካተቱላቸው ናቸው። እና ከነዚህ ገናን ጸሐፊያን እና ጽሑፎች ጋር የተካተተው "ቱሉ ፎርሳ" የብቻውን ቦታ ይዞ ልቤ ውስጥ ተጎዝጉዞ ቁጭ አለ። ጽሑፉ ደንቆኝ ደንቆኝ ሳላበቃ ጸሐፊው አለመታወቁ ደግሞ በጣም በጣም አስደነቀኝ። 


ከዛን ጊዜ ጀምሮ ልረሳው አልቻልኩም። ለምን ጸሐፊው ሊታወቅ አልቻለም? ጥያቄው ግራ ሆነብኝ። ደጋግሜ አሰብኩ ምንም የመጣልኝ ነገር የለም። እየቆየው ስለ 'ያ ትውልድ' እና (ጽሑፉ ለመጀመሪያ ጊዜ በወርሃ ነሐሴ 1968 ዓ.ም. የወጣበት ጎሕ መጽሔት) የበለጠ እያወኩ ስመጣ የተወሰኑ መላምቶች ለራሴ መስጠት ጀመርኩ። ሶስቱ የሚከተሉት ናቸው.... 


  1. ወቅቱ ጥሩ ስላልነበር... ጸሐፊው ይሄን ጽሑፍ ፅፎ ማንነቱን ከማሳወቁ በፊት ምድርን ተሰናብቶ ሊሆን ይችላል። መጽሔቱ ላይ ስራው ሲወጣ ያለ ምንም ስም ነበር። በወቅቱ የነበረው የሕዝቡ ምላሽ ግን ጸሐፊውን እኔ ነኝ እንዲል የሚገፋው ይመስለኛል። በመጀመሪያ ስራውን ያለ ስም የሰጠው ከፍራቻም (በራስ ካለመተማመንም) ሊሆን ይችላል ብዬ ስላሰብኩ ነው። 
  2. አሁንም ወቅቱ ጥሩም ስላልነበር እና በዋነኛ ሕይወቱ የሚሰራው ስራ ማንነቱን ይፋ እንዳያደርግ ገድቦት ይሆናል ብዬ አስብ ነበር። በዚ መሃል ምድርን ተሰናብቶ ሊሆን ይችላል ቀጥሎ የሚመጣው ሃሳቤ ነው። 
  3.  ጭራሽ ለእውቅና ግድ የሌለው ሰው ይሆናል። ይሄ እጅግ ጥቂቶች ጋር ያለ ባሕሪይ ቢሆንም እንኳ እንዲህ ዓይነት ለየት ያለ ስብዕና ግን አለ። ስለ ስራው የሚወራውን ይሰማል፣ በየ ቀበሌ ኪነትም ስራው በትወና መልክ ሲሰራም ሄዶ ሊያይ ሁሉ ይችላል። "እኔ ነኝ የጻፍኩት!" የማለት ግን ፍላጎቱ የለውም። ደስታውን በራሱ መስፈሪያ ልክ ተቀብሎ የጨረሰ ሰው አድርጌ እወስደዋለሁ። ስለ ስራው ሲወራ ደስ ይለዋል ሆኖም "አንተ ነህ እንዴ ጸሐፊው? ግሩም ነው! ድንቅ ነው! አጃኢብ!" መባሉ ብዙም ትርጉም አይሰጠውም። 


በህይወት ቢኖር ብዬ ስለምመኝ ለሶስተኛው መላምት እያደላው ቆየሁ። በዚ መሃል "ጸሐፊው እከሌ ነው... አይደለም እከሌ ነው... የሚሉ መላምቶችን መስማት ስጀምር የበለጠ በሶስተኛው መላምቴ ጸናው። ከሰማኋቸው ሰዎች መሃል የሚከተሉት ናቸው ሠርቅ ዳንኤል፣ ጃርሶ ኪሩቤል ሞትባይኖር እና ዳዊ ኢብራሂም ናቸው። 


በዚህ መሃል ሆኜ ነው ከጽሑፍ ይዘቱና ቴክኒኩ ተነስቼ ደራሲውን ለምን አልገምተውም ወደሚለው ሃሳብ የመጣሁት። ግምቴ ያረፈበት ሰው ደሞ ሰለሞን ለማ ይባላል። ከዚ ተነስቼ ነው "የቱሉ ፎርሳን ደራሲ እኔ እንደምገምተው..." የሚል ረዘም ያለ ጽሑፍ 2012 ላይ የጻፍኩት። ይሄ ጽሑፍ እንግዲህ ለሀሳቤ በእጅጉ በጣም ጠቅሞኛል። ከቱሉ ፎርሳ ጋር የተያያዘ አዲስ መረጃ ሲኖራቸው ሰዎች ቶሎ ያሳውቁኛል። አንድ ሁለት ቢሆኑም እንደኔ መላምታቸውን ያስቀመጡ ሰዎችም አይቻለሁ። 


ቀጣይ የማነሳቸው ሁለት ሰዎችንም መጀመሪያ በሰው ጥቆማ ነው ያወኳቸው። እስከዛሬ ካየኋቸው ፅሁፎች ሁሉ ስለ ቱሉ ፎርሳ 'ደራሲ' በመጽሐፍ መልክ ተጽፎ ያየሁት በቀጣዮቹ ሁለት መጻሕፍት ብቻ ነው። ሌላ ካለ መረጃው ስለሌለኝ ነው። ሁለቱንም መጻሕፍት እናያቸዋለን። 



የመጀመሪያው በመሐመድ ይማም 2006 (2013) የታተመ Wore Negari: A Memoir of an Ethiopian Youth in the Turbulent '70s የሚል እንግሊዝኛ መጽሐፍ ነው። 


ከዚ ጽሑፍ ጋር በሚስማማ መልኩ ነገሩን ለማሳጠር የመጽሐፉ ጸሐፊ መሐመድ ይማም ጎሕ መጽሔት በኤዲተርነት ይሰራ የነበረ ግለሰብ ነው። ስለዚህ ለቱሉ ፎርሳ ከሱ የበለጠ የሚቀርብ የለምና ነገሩን ለመስማት ሰፍ ማለታችን አይቀርም። በሚያሳዝን ሁኔታ ግን ብዙ የተብራራ መረጃ አልያዘም መጽሐፉ። ከቱሉ ፎርሳ ርዕስ ውጪ ሌላ የምፈልጋቸው መረጃዎችን ግን በግል ከመጽሐፉ አግኝቼበታለሁ። ስለዚህ ጸሐፊውን እጅግ ከልብ አመስግኜ ነው የምጀምረው። 


መጽሐፉ የሚያነሳቸው መረጃዎች የሚከተሉት ናቸው.... 


  1. የቱሉ ፎርሳ ደራሲ ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ድግሪ አለው። (ገፅ 79) 
  2. አቃቂ ከሚገኙ የኢንዱስትሪ ዞኖች ውስጥ በአንዱ፣ በአስተዳዳሪነት ደረጃ ይሰራ ነበር። (ገፅ 79) 
  3. ቱሉ ፎርሳ ጽሑፉ ሶስት ክፍል ነበረው። ክፍል ሁለትና ሶስት በሳንሱር ምክንያት ሳይታተሙ ቀርተዋል። (ገፅ 79) 
  4. EPRP (ኢሕአፓ) ላይ ለሚሰነዘሩ የጋዜጣ ጽሑፎች መልስ እንዲሰጥ የተዘጋጀ 'ጊዜያዊ ኮሚቴ' ውስጥ የቱሉ ፎርሳ ደራሲ አንዱ አባል ነበር። (ገፅ 101) 


የመጽሐፉ ጸሐፊ መሐመድ ይማምም የዚህ ኮሚቴ አባል ከነበሩ ሶስት ሰዎች መሐል አንዱ ነበር። መሐመድ ይማም - የቱሉ ፎርሳ ደራሲ አንዱ የኮሚቴ አባል መሆኑን የለየው - በእጅ ጽሑፉ እና በጽሑፍ ስታይሉ መሆኑን ይነግረናል። የጎሕ ኤዲተር ስለነበር ይሄን ለማመን አንቸገርም። ግን ገፋ አድርጎ አያብራራውም። 


መሐመድ ይማም ከላይ ቁጥር አንድ እና ሁለት ስለሰፈሩት ነገሮች ምንም ዓይነት መረጃ አልሰጠንም። የቱሉ ፎርሳ ደራሲ ከአዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ድግሪ እንዳለው ያወቀበትን መንገድ ጭሩሱኑ አላወቅንም። ሁለተኛውንም መረጃ እንደዛው። 


ምናልባት - የኔ ግምት ነው... ቁጥር 4 ላይ በሰፈረው የጊዜያዊ ኮሚቴ አባልነት ጊዜ ማለት ነው... የሰውዬውን መረጃ ከዛ አግኝቶ ሊሆን ይችላል። ሆኖም እንደዚህ ነው ብሎ ስላልነገረን መረጃውን እንደ የተጣራ መረጃ ለመውሰድ የሚያስችል ድፈረት እንዳይኖረን ያረገናል። 


መጽሐፉ ሌላ ቦታ ላይ ደግሞ... መሐመድ ይማም የላብ አደር ጋዜጣ 'ኤዲቶሪያል ቦርድ' ሆኖ መታጨቱን ሲነግረን... አሁንም የኤዲቶሪያል ኮሚቴ አባላቱ ከሱ ጋር ሶስት ናቸው። አንደኛው ወልደአብ ሲባል እዚህም ሶስተኛው ሰው ተብሎ የተገለፀ ሌላ ሰው አለ። ይህም ሰው የተገለፀው "አንድ ብሔራዊ ፋብሪካ ውስጥ በአስተዳዳሪነት ደረጃ የሚሰራ ሰው ነው" ተብሎ ነው። ይሄ አገላለፅ ሲደጋገም ግራ ይገባል። (ገፅ 97 እና 98) 


ለጊዜው ይሄን መጽሐፍ እዚህ እንተወውና ወደ ሁለተኛው መጽሐፍ እንለፍ። ወደ ኋላ እንመለስበታለን...

 


ሁለተኛው፣ በኮሎኔል ፈቃደ ገብረየስ ተጽፎ በ2015 ዓ.ም. የታተመ "የኔ መንገድ" የተሰኘ ግለ ታሪክ መጽሐፍ ነው። እዚህ መጽሐፍ ላይ ገፅ 106 ላይ "ታረቀኝ በዳሣ - ያልተዘመረለት ጓደኛዬ" የሚል ንዑስ ርዕስ አለ። ገፅ 106 የጀመረው ይሄ ጽሑፍ እስከ ገፅ 116 ድረስ ስለ ታረቀኝ በዳሣ እያወራ ይቀጥላልል። 


ታረቀኝ ሻውል ደማ ትምህርት ቤት በመምህርነት ያገለግል ነበር። ከመጽሐፉ ጸሐፊ ኮሎኔል ፈቃደ ጋርም ትውውቃቸው እዛ ትምህርት ቤት ነው የሚጀምረው። በነዚህ አጭር ገጾች የተገለፀውን ታረቀኝ አንብበን ስንጨርስ ሁለት ነገር የሚሰማን ይመስለኛል። አንድ ነፍሳችን ለታረቀኝ አብዝታ ታዝናለች። አንድም ብዙ ስለሱ ሰፋ አድርገን ማወቅ እንፈልጋለን። እኔ እንደዛ ነው የተሰማኝ። የታረቀኝ ዓይነት ሰዎች ሁሌም ሲያልፉ ነው የሚታወሱት። የተለዩ ስለሆኑ ለእይታ ግድ የላቸውም። የሚያሳዝነው ግን እምቅ ችሎታቸው፣ ስውር ስራቸው ውስን ቦታ ተቀምጦ መቅረቱ ብቻ ነው። እንደ ታረቀኝ ያሉ ሰዎች በእርግጠኝነት በቁም እያሉ ለሰው ሳያሳዩ የሰሩት ቀሪ ስራ ይኖራቸዋል። ሆኖም ስራቸውን ካለፉ በኋላ ቆይቶ፣ አንድ አስተዋይ ሰው ወይ ልብ ይለዋል አልያም እንደ ቆሻሻ ነገር ተጥሎ ይቀራል። ይሄ እጅጉን የሚያሳዝን ነገር ነው። 


ኮሎኔል ፈቃደ ገብረየስ ታረቀኝ በዳሣን ስብዕናውን በደንብ እንዳስተዋሉት ማሳያ ጽሑፋቸውን ላቅርብ <<እነዚህ በሥነጽሑፍ እና በፍልስፍናው ዓለም የተራቀቁ ሰዎች ዓለምን የሚለውጥ ግሩም ሥራ እየሰሩ፣ ለራሳቸው ግድ የማጣቸው ነገር ግራ እንደ ሆነብኝ አለ።>> ገፅ 112..... በቃ እነ ታረቀኝ ብዙውን ጊዜ እንደዚ ስለሆኑ ይመስለኛል። 'በቃ ናቸዋ!' ከማለት ውጪ ሌላ ማብራሪያ ለጊዜው አይታየኝም። 


ባነበብኩት ጽሑፍ ታረቀኝ ከፍ ብሎ፣ ጎልቶ፣ ደምቆ ነው የታየኝ። በነገራችን ላይ የ90ዎቹ ትውልድ ታረቀኝ በዳሣን በስሙ ባያስታውሰው እንኳ በአንድ ድርሰት ስራው ግን ፈፅሞ ሊዘነጋው እንደማይችል አምናለሁ። "ሶስቱ ወፎች" የተሰኘው የቴሌቪዥን ድራማ በታረቀኝ ከተሰሩ ስራዎች ውስጥ አንደኛው ነው። በዚህም አጋጣሚ ያልተዘመረለት ጓደኛቸውን ያነሱት ኮሎኔል ፈቃደን ከልብ አመስግኛቸው ልለፍ። ከተቻላቸውም ስለ ታረቀኝ ሰፋ አድርገው ያስነብቡን ዘንድ ምኞቴን ገልጬ ወደተነሳንበት ጉዳይ ልመለስ። 


ወደ ቱሉ ፎርሳችን ስንመለስ፣ እንደ ኮሎኔል ፈቃደ መጽሐፍ ሃሳብ የቱሉ ፎርሳ ደራሲ ከላይ የተነሳው ታረቀኝ በዳሣ ነው። ቢሆንና የበለጠ ነፍሱ በዚም ብትዘከር ከኔ በላይ ጮቤ የሚረግጥ ሰው አይኖርም ነበር። ግን በሚያሳዝን ሁኔታ ይሄም መጽሐፍ እንደ መጀመሪያው መጽሐፍ የጠራ መረጃ የለውም። መረጃዎቹን እናያቸዋለን። 


ከገፅ 107 ስንጀምር ይህ ፅሁፍ ሰፍሯል። <<በተለይ በአብዮቱ ወቅት የደርግን ብልሹ አሠራሮችን የሚያወግዙ ሥነ ግጥሞችን በጎኅ መፅሄት ላይ በብዕር ስም ያወጣ እንደነበር አስታውሳለሁ። መፅሄቱ ከወጣ በኋላ የኔ ነው ሳይል እያነበበ ይህንስ አነበባችሁት እንዴት አገኛችሁት ይለን ነበር። ይህች የራሱ ነች ማለት ነው ብለን እናነበዋለን። የግጥም አጣጣሉ ደግሞ ለየት ያለ ስለነበር የርሱ መሆኑን ማወቅ አይከብድም። የርሱ ነው ብለን እንጠረጥራለን። ባንድ ወቅት በብዕር ስም የፃፋቸውን ግጥሞችና ልብወለድ ፅሁፎች ለተወሰንን ጓደኞቹ አጫውቶን ነበር።>> 


ከላይ ያለው ጽሑፍ ምናልባት ለእርግጠኝነት የተጠጋ መላምት እንለው ይሆናል እንጂ ሙሉ ተጨባጭ ማስረጃ ሊሆን አይችልም። ከላይ የቀረቡት ሁለት አገላለፆች በራሳቸው መላምቱ ጥርጣሬ ላይ መመስረቱን ያሳያሉ። "ይህች የራሱ ነች ማለት ነው...." እና "የርሱ ነው ብለን እንጠረጥራለን" ግልፅ መልእክቶች ናቸው። የመጨረሻውም መስመር "ባንድ ወቅት በብዕር ስም የፃፋቸውን ግጥሞችና ልብወለድ ፅሁፎች ለተወሰንን ጓደኞቹ አጫውቶን ነበር።" የሚለው የተብራራ ነገር የሌለው ድፍን ያለ ነገር ነው። 


በነገራችን ላይ በዚ የተነሳ ታረቀኝ የቱሉ ፎርሳ ደራሲ አይደለም እያልኩ አይደለም። ሊሆንም ይችላል። ግን መረጃው በቀረበበት መንገድ፣ ነው ብለን መደምደም አንችልም ነው እያልኩ ያለሁት። በተጨማሪም ኮሎኔል ፈቃደን እና ጓደኞቻቸውን በደንብ ነው የምረዳቸው። የታረቀኝ ዓይነት ሰው ስለ ራሱ የማውራት ዝንባሌውም፣ ስለ ራሱ ያለውም ነገር ከሰው ስለሚለይ፣ ለመላምት እና ለጥርጣሬ ቢዳረጉ አልፈርድባቸውም። አሁንም ነፍሴ ምናለ እሱ በሆነ ጸሐፊው ብላ እንደተመኘች ነው። እንቀጥላለን... 


ገፅ 108 ላይ ስንደርስ .... 


የታረቀኝ በዳሣ አንድ የልብ ወለድና አንድ የሥነ ግጥም ስራው ተቀንጭቦ ቀርቧል። ግጥሙ "አበራ ገሙ" ሲሆን ልብወለዱ ደግሞ "ቱሉ ፎርሳ" ነው። ይሄም ምንም ማስረጃ የቀረበበት ነገር አይደለም። መነሻው ከላይ የቀረበው መላምት ይመስለኛል። ከዚ መረጃ ተነስተን ነገሮችን ማስፋት እንጀምራለን።  


በመጀመሪያ ስለ ጎሕ መጽሔት የብዕር ስሞች ብናይ፣ ከአንድ በላይ የሆኑ የብዕር ስሞች አሉ። ለምሳሌ ለኃይሌ ፊዳ "ዲያሌክቲካዊና የታሪክ ቁስ አካልነት" መጽሐፍ ሂስ የሰራው "አደፍርስ" የሚለው ስም ከአንድም ሁለት ሰዎች የተጠቀሙበት የብዕር ስም ነው። ብርሃኑ እጅጉ እና ዮሐንስ አረቡ (ዮሐንስ ብርሃኔ) አደፍርስ የሚለውን የብዕር ስም በተለያየ ጊዜ ተጠቅመውበታል። ሌላም የብዕር ስሞች ጎሕ መጽሔት ላይ ነበሩ። ግን ጎላ ተብሎ የሚታወቀው የብዕር ስም እሳቱ ተሰማ ነው። 


እናም "አበራ ገሙ"ን የጻፈው እሳቱ ተሰማ ነው። ስለዚህ በኮሎኔል ፈቃደ ሃሳብ ስንሄድ እሳቱ ተሰማ ታረቀኝ በዳሣ ነው ማለት ነው። ነው ብለን እንቀጥልና.... አበራ ገሙና ቱሉ ፎርሳ ጎሕ መጽሔት በአንድ እትም ላይ በተከታታይ ገፅ የወጡ ስራዎች ናቸው። አንደኛው በብዕር ስም አንደኛው ያለምንም ስም። ሊሆን የሚችልበት መንገድ ቢኖርም ለምን ማለታችን ግን አይቀርም። 


እስቲ ቀጥለን እሳቱ ተሰማ የሚለው ብዕር ስም ባለኝ መረጃ መሰረት ማነው የሚለውን እንይ። ከላይ ወደጀመርነው መሐመድ ይማም "Wore Negari: A Memoir of an Ethiopian Youth in the Turbulent '70s" እንመለስ። 


መሐመድ ይማም እሳቱ ተሰማን እና የቱሉ ፎረሳን ደራሲ ሁለት የተለያዩ ሰዎች አድርጎ ነው የሚገልፃቸው። የቱሉ ፎርሳን ጸሐፊ የእጅ ጽሑፍን በደንብ እንደሚያውቀው ስለፃፈ ከእሳቱ ተሰማ ጋር መመሳሰሉ አልታየውም ማለት ነው። ይሄን በቃ ድንገት ልብ ሳይለው ቀርቶ ነው ብንል እንኳ የተለያዩ ቦታዎች ላይ ሁለቱን ጸሐፊዎች ፍፁም ለያይቶ ነው ያነሳቸው። 


እንደውም እሳቱ ተሰማን በአካል ያውቀዋል። ስለ እሳቱ ተሰማ ሲጀምር "ጸጋዬ ብዕርህ ይሙት" የሚለው ፅሁፉ ጎሕን ተነባቢ እንዳደረጋት ገልፆ ብዙ ግጥሞቹንም በክብር ተቀብለው እንዳስተናገዱለት ያስከትላል። አዲስአበባ እያሉ ሊረሳው የማይችለው የእሳቱ ተሰማ ቅፅፈታዊ እይታ ስለነበረው፣ በፈረንጆች 1980ዎቹ መጀመሪያ ላይ አሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ በአካል እንዳገኘውም ይነግረናል። ወሬውን ስናሳጥረው፣ መሐመድ ይማም እሳቱ ያለበት ድረስ ተከትሎ ተዋውቆት፣ የት እንደሚያውቀው ሲነግረው እሳቱ ተሰማ ብዙም የማውራት ፍላጎቱ ስለሌለው ወሬያቸው በአጭር የተቀጨ ይሆናል። እሳቱ መጀመሪያ መሐመድን እንደማያውቀው ነግሮት ነበር። ገፅ 77 እና 78 


ለኛ ግን አንድ ተጨማሪ መረጃ ሰቶናል ማለት ነው። እሳቱ ተሰማ በፈረንጆች 1980ዎቹ መጀመሪያ አሜሪካ ነበር ማለት ነው። ወደ ኮሎኔል ፈቃደ መጽሐፍ ስንመለስ ቀጣዩን ጽሑፍ እናገኛለን። << "ታረቀኝ በዳሣ" .... ለሥራና ለአጭር ጊዜ ሥልጠና ወደ ተለያዩ ሀገሮች ለምሳሌ ግብፅ፤ ምሥራቅ ጀርመን፤ እንግሊዝ ወዘተ... ተጉዟል>> ገፅ 114 አሜሪካ ወዘተ ውስጥ ተካታ ካልሆነ በቀር የለችም። ይሄም ልባችንን እንዳንጠጠለው ይቀራል ማለት ነው። 


አንድ በጣም የገረመኝ ነገር መሐመድ ይማምም ሌላ ቀጥሎ የማነሳውም ሰው እሳቱ ተሰማ የብዕር ስም መሆኑን ነግረውን እንትና ነው ብለው ግልፅ ማረግ አለመፈለጋቸው ነው። 


ስለዚህ እስካሁን ባለው ሃሳቤ ከተግባባን ታረቀኝ በዳሣ እና እሳቱ ተሰማ አንድ ናቸውም አንድ አይደሉምም የምንልበት ምንም የሚጨበጥ መረጃ የለንም ማለት ነው። ታረቀኝ በዳሣም የቱሉ ፎርሳ ደራሲ ነውም አይደለምም፣ ማለትም የምንችልበት መሬት የረገጠ ነገር የለንም። 


ሆኖም እሳቱ ተሰማ ማን እንደነበር ማወቅ የምንችል ይመስለኛል። ከላይ ቀንጨብ አድርጌ ያነሳሁት ሰው ነቢይ መኮንን ነው። ነቢይ የጨዋታ እንግዳ ሆኖ መዓዛ ጋር ቀርቦ ነበር። ሶስተኛው ሳምንት የመጀመሪያው ክፍል ላይ ስለ እሳቱ ተሰማ የሚያወራበት ክፍል አለ። እሳቱ ተሰማን በአካል ያውቀዋል። ከመሐመድ ይማም ቀጥሎ ሁለተኛ ሰው ማለት ነው ለኔ። ስለዚ ለዘመኑ ሰዎች እሳቱ ተሰማ በደንብ የሚታወቅ ሰው ይመስለኛል። ነቢይም ሲያወራ ግን እሳቱ እኮ እንትና ነው የማለት ፍላጎት አላየሁበትም። ይሄ ገርሞኛል። 


በግል ሶሻል ሚዲያ ስለማልጠቀም እንጂ እሳቱ በቶሎ የሚታወቅ ሰው ሊሆን እንደሚችል ይሰማኛል። የጨዋታ እንግዳ 4ኛው ሳምንት ክፍል ሁለት ላይ መዓዚ ስትጀምር እንዲህ ትላለች <<ነቢይ እስቲ እንደገና አሁን ኢሕአፓ ውስጥ ማን መለመለህ? እሳቱ ተሰማ? ነው ወይንስ ?...>> ስትል ፈጥኖ "ሌላ ሰው" ይላታል። መዓዚ ራሱ ቀድመው ካወሩት ተነስታ ብቻ ሳይሆን እሳቱን እሷም የምታውቀው መስሎ ተሰምቶኛል። ከተሳሳትኩ ታራሚ ነኝ። ማለት የፈለኩት ግን 'እሳቱ ተሰማ የሚታወቅ ሰው ነው' ማለት ነው። እና የምታውቁት ሰዎች ብታሳውቁኝ ብዙ ብዥታ ታጠራላችሁ ማለት ነው። ቢያንስ የፍለጋ ስራችንን እያጠበብነው እንመጣለን። ያለዚያህ ግን የዲፒ ሽንዴን "ፍለጋው አያልቅም..." የሚለውን ዘፈን እየዘፈንን ማዝገም ነው ዕድላችን። 


አሁን ደግሞ ስለ ቱሉ ፎረሳ ሶስት ክፍልነት እናንሳ። መሐመድ ይማም እንደነገረን ክፍል ሁለት እና ሶስት በሳንሱር ምክንያት አልታተሙም። (ያ የሚሆነው ካልተሳሳትኩ 1968 እና 1969 መሆኑ ነው)። ሆኖም ግን በግል ባረኩት ፍለጋ መሰረት (ነሐሴ 1984 - መስከረም 1985) እትም ላይ "ፎርሳ ብላሽ" በሚል ርዕስ ከ17 ዓመታት በኋላ የተፃፈ የቱሉ ፎርሳ ቀጣይ ክፍል ሌላ ፅሁፍ አግኝቻለሁ። ጽሑፉን እዚሁ ዌብሳይት ላይ ስላጋራሁት ሊንኩን ተጭናችሁ ማንበብ ትችላላችሁ። በነገራችን ላይ (ነሐሴ 1984 - መስከረም 1985) ሁለት የተለያየ ወር እትም ሳይሆን የአንድ ወር አንድ እትም ነው። 


'ፎርሳ ብላሽ' የሚለው ጽሑፍ 'ይቀጥላል' ብሎ ነው የሚያበቃው። ቀጣዩ ክፍል ሊኖርበት የሚችለውን መጽሔት ግን የትም ላገኘው አልቻልኩም። ወመዘክር በሁለት አመት ውስጥ እጅግ ለተለያየ ጊዜያት አስፈልጌዋለሁ ግን (ነሐሴ 1984 - መስከረም 1985) ብሎ (የካቲት 1985) የሚል የጎሕ እትም ብቻ ነው ያለው። ስለዚህ ቀጣዩን ክፍል ላገኘው አልቻልኩም። መጽሔቱ ወመዘክር የሌለበት ምክንያት ሁለት ሊሆን ይችላል። አንድ - ከመስከረም እሰከ የካቲት በመሃል የታተሙት ወመዘክር አልገቡም። ሁለት - በዛ ወቅት ውስጥ ጎሕ ጭራሽ አልታተመም ነበር። ፎርሳ ብላሽም ግን ሌላ የተለየ የዘመን እይታ ነበረው። ግን ባላለቀ ነገር ብዙ ማውራት ተገቢ ስላልሆነ እዚሁ ላቁመው። 


እንደ መውጫ:- ነቢይ እና እሳቱ ተሰማ ከተነሱ አይቀር ግን በደረቁ ላለመውጣት ከመዓዚ ጋር ካወሩት ላይ የግጥሙን መንፈስ አንስቼው ላብቃ። 


የጨዋታ እንግዳ ሶስተኛ ሳምንት የመጀመሪያው ክፍል ላይ ያለ ንግግር ነው። ነቢይ ነው የሚያወራው 


<<አሁን ዘመቻ ጣቢያ ያገኘሁት እሳቱ ተሰማ የሚባለው ገጣሚ፣ የጎሕ ገጣሚ ነው። እውነተኛ ስሙ አይደለም ያው የብዕር ስሙ ነው። እሳቱ ተሰማን እዛ ሳገኘው... በርግጥ በኋላ ነው ያወቅትኩት እሳቱ መሆኑን፤ እንዲሁ ስናወራ እንደዚህ ስንጫወት ነበር። እና በጣም ከራር ጸሐፊ ነው። በጣም ሀይለኛ ቃላት ነው የሚጠቀመው። እና ደግሞ አብዮታዊ ድፍረት አለው። የነበረው ነው ያን ጊዜ። ያኔ "ጸጋዬ ሙት፣ ብዕርህ ይሙት" ብሎ የጻፈው ነው። እንግዲህ ከዘመን በኋላ። Almost ከ35 አመት በኋላ፣ እርግማኔን መልስልኝ የሚል ግጥም ጽፎ ይቅርታ ጠይቋል።>> 


ወደ 'እርግማኔን መልስልኝ' ከመሄዳችን በፊት መጀመሪያ የእሳቱ ተሰማን ጸጋዬ ብዕርህ ይሙት ያለበትን የእርግማን ግጥም ከጎሕ መጽሔት ላይ ያገኘሁትን ላጋራቹና ወደ ነቢይ መኮንን እንመለሳለን። 


****** ፀጋዬ ያንተ ብዕር — እሳቱ ተሰማ 1968 **** 


ብዕርህ ጐልድፎ « ሞቶ » 

ወዳጅህ . . . እርሙን አውጥቶ 

አሻሮ ተድሶለት 

እንኩሮ ተነኩሮለት . . .

ነፍጠኛው ባሕል ጉልታዊው 

ቡርዥው ቅይጡ . . .« ሙላቶው » 

ለሞተለት ስንብቱ 

አርባ—ተዝካር — ሙት ዓመቱ ! 

« የዕመቀ ዕምቃት ዕርገት 

እንደዕምነቱ ይሥመርለት » 

የለቀስተኛው « ምርቃ » 

ጉንጭ በሚያስጠባ ሲቃ 

ሲጠለዝ . . . ሲደቃ ደረት 

ሙሾ ተደርድሮለት 

እንዲህ አልፎ ተቀብሮ 

ምድረ — አድሀሪ አንጀቱ አርሮ 

ጭቁኑ ሕዝብ ፈንጥዞ 

መሰል ኪነቱን መዞ 

የአብዮት ልጅ ጃኖ ለብሶ 

መቃብሩ ላይ ነገሶ 

የትግል ገሪሳ ሲናገር 

« ሙት — ብዕር ሊቆም ቢጥር 

በእጁ በእግሩ ቢውተረተር 

ነፍስ ሊዘራ ቢፍጨረጨር 

ትርው — ትርው . . . ደንበር—ገተር ። 

ቋት ላይሞላ . . . ጠብ ላይል 

ሄዶ ላይሄድ . . .በስሎ ላይበስል 

« ወፌ ቆሞች » . . . ላንተ ቀለም 

የሕልም — እንጀራ ከንቱ ሕመም 

ጸጋዬ . . . ብዕርህ « ይሙት » 

         አልፎበታል ይለፍበት 

         ጸጋዬ ሙት ይከተት 

« ላማ ሰበቅታኒ » አትበል 

         ለማንም አንተውህ 

ከቆምክለት ሥርዓት ጋር 

         ገነጣጥለን ሳናነኩትህ 

እንዲያው በግላጭ ተብከንከን 

         እሪ — በል አንቧርቅ . . . እጓራ 

ቋንቋችንም ለየቅል ነው 

         ያንተ ቀኝ ፤ የእኛ ግራ ! 


ቁርበት እንጥፉልኝን . . .

         ለማያውቅህ ተርትለት 


ላብ አደር . . . አርሶ አደሩ 

         ሚናህ ተከስቶለት ! 

ይልቅስ « ጎድን » ብለናል 

         ጆሮ ካለህ መንገድ ልቀቅ ! 


« ያንኪ » ቱሪስትን ብላ 

         እንዳትወርድ እመቀመቅ !  


«ሂዱ » ያልነው የእድገት ችቦ ፤ . . .

          የማን ነገረ — ፈጅ ነህ ? 

እረ ማን ይልህ . . . ማን አበሰህ ? 


          ማን አዝማችነት « ቀባህ » ? 


ይህ እራስህን ማሞካሸት 

           
አሁንም አልጠፈፈልህ ? 


የ« ደጃዝማቾች » ንግርት . . .

           አሁንም አልጠገገልህ ? 


የፊውዶ — ቡርዥ ዘኬ . . .


           በገፍ ዝቆ — በገፍ ቅሞ 

የፀጋዬ የኪነት ድጥ . . . 

           አሁንም ላበላው ታሞ ! 


« ማነሽ ባለሳምንት ? . . . 

           ያስጠምድሽ ባስራስምንት » 

ብሶትሽን ጭንቀትሽን . . .. .

           ጸጋዬ የሚከትባት ! 


« ማነህሳ ባለሳምንት ? 

« ማነህሳ ባለሳምንት » ? 

            ለጸጋዬ የብዕር ዶፍ 

« ጠበል—ጠዲቅ ዘካሪ » 

            በሞትኩ የምትል እንከፍ !

የገዥው መደብ ገጣሚ . . .

ውጋት ቁርጠቱን አጋሚ 

እኔስ ቀለምህ አልቋል 

የብልቃጥህ ጡቱ ነጥፍዋል 

ጠውልጓል . . . ታልቦ አልቋል ብዬ 

አሁንም አለህ ጸጋዬ ? 

አሁን . . . ለላብ— አደሩ 


ለጭቁኑ . . . ለአርሶ — አደሩ 

በአብዮት ወቅት ለአብዮት 


እውን . . . ብዕርህ ሊከሰት ? 


ነጭ — ብራና ሊያጠቋቁር 

          « ሙት — ብዕርህ » ሲንከላወስ 

ሳያንሰራራ በፊት . . .

           ያስፈልጋልና ሂስ 

ተራማጅ ዘማች ዘማቾች 


           « ሂዱ » አልናቸው የምትለው 

የገጠር ተልእኮአቸውን . . . .


            ማንም ክትባት አልከተበው ! 

የመደብ ትግሉ እንዲከር 

            ቅራኒው እንዲፋተግ 


ጭሰኛው እንዲሰላ 

            ንቃቱ እንዲንቦገቦግ 

የአርሶ አደሩን መመሪያ 


            ከአርሶ አደሩ ጋር ነድፈው 

ጭንቀቱን ጭንቀታቸው 


             ጠላቱን ጠላቴ ብለው 

የሁለት ጠላት መንታ በትር 

              ከየአቅጣጫው ወርዶባቸው 


ከሚችሉበት ደረጃ

              ባዶ እጃቸውን ደርሰው . . . 

ከሚወዳቸው ሕዝብ ጋር 

               ተቃቅረው እንዲጣሉ 


አሉባልታው ሲዘራ . . .

                እንዲጠሉ . . . እንዲቀሉ . . .

አብዮት — ፈንጋይ ኃይሎች 


                 « ጸጋዬ » እንዳንተ ያሉቱ 

እንደ « እርያ ሲያስጐበብቱ . . . 

 . . . . በዘይት ሲያለተልቱ . . . » 

ለጦረኛ ምላሳቸው 

                ጆሮዋቸውን ዳቦ አልብሰው 

ታስረው ተገርፈው ተሰቅለው . . . 

                እንዲያ ለፍተው — እንዲያ ሞተወ 


« ከትግል ፈርጣጭ ብኩኖች . . . »


               ሌላም ስንቱን ተብለው

               የገጠሩን ጭሰኛ ጡት 


               አቆራራጭ ለመቀባት 


ስንቱ ተነስቶ . . . ተቦክቶ 

                ስንቱ በኖ . . . ስንቱ ባክኖ 

እልፍ ቋጥኝ ዘላለው 

                ስንቱን ወንዝ ተሻግረው 


ፊታቸውን ቢያዞሩ . . . . 


                « ዕርቃናችንን » ነን ብለው

« . . . ይታጠቅ ይደራጅ እንጂ 

               አርሶ — አደሩ አፈር ገፊው


የራሱን ሞት ይሞታል . . .


                ሞግዚትም አያስፈልግም


ከሽንገላው ከድላላው 


                በአፍ ከሚያመፃድቁት 


ወዳጅ ነን ባዮች ሁሉ . . .


                ሳይውል ሳያድር ያስታጥቁአት . . .


ብለው ዘማች ዘማቺት 

                ሲጮኹና ሲጣሩ


እረ ጸጋዬ ብዕሮችህ . . . 

                ወዴት አገር ነበሩ ? 

ቢጤዎችሀ . . . ከተሜዎች » 

ከእነርሱም ውስጥ አድር — ባዮች 

ስትክዱ ልጆቻችሁን 

                ስታዘዙ እጃቸውን 

ሲታሰር የአብራካችሁ 


ሊታይ ታማኝነታችሁ ? 


የማይመስለው መስሏችሁ ! 


ያልሆንክ መሰለህ የሆንከውን 

                
ለምን ? ጸጋዬ . . . ለምን ? 


                ትሸፍጣለህ አሁን ? 


                 « ሒዱ » ማለት ፤ ሑሩ ማለት 

                 ሙት ማለት . . . « ማሠማራት » 


ማግለል ማሸሽ ታውቃላችሁ 

                ከዳር ቆሞ ማበጠር 


« ነፋስ መስጠት » ሙያችሁ ነው 


                ብስል ፍሬ መጠርጠር። 


                አዎን ጸጋዬ አምነሃል 

                ልባችሁ ባልደረሰበት 

ቀልባችሁ ባላረፈበት . . . 

                ዓይናችሁ ባልገበየበት 

« ሔዱ ባላችሁት ሳይሆን . . . 

                የአብዮት ግዴታው ሆኖ 

ዘማች ገድለ — ብዙ ነው 

                በጧት — በቀን — በሌት ባዝኖ ! 

ዋጋህን አውቀሃልና . . . 

                « . . . ቀና ዘንበል » ማለትህን 

                « ወሬ መሸቀል » ህን 

                
« መተት ማብከልከል . . . » ህን 

ከዚህ በላይ ካንተ አንሻም 

                አራት ነጥብ አድርግበት 

ጸጋዬ በዚህ ያክትም 

                ግሣንግሱ ያንተ ኮተት ! 

                እንደ እርያ ማስጐስበት ! 

« ይታዘንልህ » ይገባል


          . . . የከተማው ባይተዋር 


ተራማጁ ንዑስ ሆነ 

                አብዮታዊው ምሁር 

ለዲስኩቴክ — ሪቺ . . . ፈሊጥ 

                ሳይደለል ሳይበገር 

ሽንጡን አሥሮ . . . ባጭር ታጥቆ 

የሸሚዙን እጅጌ . . . . ጠቅልሎና ሰቅስቆ 

ጥሮ — ግሮ ላስተማረው 

ለሳይንስ ጐሕ ላበቃው 

ገጠር ያለው በገጠር 

ውለታ ሊመልስ ሲጥር 

የከተማው በከተማ 


ዘር ሲዘራ . . . ሲያለማ 

ለእንዱስትሪው ላብ አደር 

                የታሪክ የታሪክ ተልእኮውን 

የመደብ ትግሉን ድግስ . . .  

                የንቃቱን የትጥቁን 


                 — « ጋሬጣውን አሜከላውን » 

                 ማበጠሪያ መነጽሩን

                 . . . ማርክሲዝም ሌኒኒዝምን 

ሳይሰለች . . . ሳይታክት ተግቶ 

አብሮት ደክሞ አብሮት ሞቶ 

አብሮ ታስሮ . . . ተሰቃይቶ 

ይደራጃል . . . ያደራጃል 

ያነቃቃል . . . ይታገላል 

                ግንባር — ቀደም . . . ላብ — አደሩ 

እንዲቆራኝ ከአርሶ — አደሩ 

ከመደብ ትግል አጋሩ 

ያሳውቃል ያሳብራል ! 

መች እንደ አንተ ጸጋዬ . . . 


                ቀናና ዘንበል ይላል ? 

                የመንደር ወሬ ይሸቅላል ? 

                ቦዝኖ ያውደለድላል ? 

ሆኖም ለማያውቅ ሰው . . . 

                 ተምሮም ለደነቆረ 


ለመደቡ ፣ ለጥቅሙ ሲል 

                አጉል ሸንጡን ለገተረ 

ፋብሪካ . . . ኢንዱስትሪዎች 

ት/ቤት . . . ሆስፒታሎች 

ምርት አካፋይ ድርጅቶች 


የሙያ ማህበሮች 

የቀበሌ ማህበሮች 

የወጣቶች ማኅበሮች 

የምዝብር ሕዝብ ከምችቶች . . . 

. . . ሌሎችም ጭቁን ሕዝቦችን 

                ባቀፉ ከተማዎች . . .

ከወሬ መሸቀል በቀር 

                ከማውደልደል ከማብከልከል 

ዓይኖቹ ታውረው የለ ?

                ሌላ ምን ይታየዋል ! 

ቢዘሩስ ቢቅበዘበዙ 

                እንይ ብለው ቢቃትቱ 

ቀልባቸውን የሚስበው 

                የመደባቸውን ግሽበቱ ! 

ወሬ ማንፈስ መሸቀሉ 

ማውደልደል መብከልከሉ ! 

« ልማድ ያው አጓዙ ብዙ ናት 

                ብቻዋን መሄድ ባታውቅም 

                ያዘላትን ባታስቀድም 

                እንጂ መሄድስ አይቀርም . . .» 

                ታዲያስ ያንተስ እከክ 

                ወዴት ታከክ ? ወዴት ለከክ ? 

ለታነጸ ለታሰበ 

ጭቁኑን ሕዝብ ላቀረበ 

ከተማም ፍጹም አምባናት

ለትግል . . . ለአብዮት ! 

— ላብ — አደሩ ፣ አርሶ — አደሩ 

ተራማጅ ምሁሩ . . . 

ይደራጃል ይታጠቃል 

ድሉም የርሱ ይሆናል 

የፓሪስ ኮሚዮን ያብባል 

               ከዊን አጽናፍ ይረብባል 

ገና ምኑን አይተሃል ! 

              ጸጋዬ ያንተ ብዕር 

              ምንም ባቦዝ . . . ቢጠራጠር 


               የታሪክን ሐቅ አይቀይር 

               ጭቁን ሕዝብ ፈንጥዞ 

                መሰል ኪነቱን መዞ 

                የአብዮት ገሪሳ ሲገር 


                « ሙት — ብዕር » ሊቆም ቢጥር 

                በእጅ በእግሩ ቢውተረተር 

                 ትርው — ትርው . . ደንበር — ገተር 

                 የጉም ፡ ጭበጥ ለፍቶ — መና 

                 . . . የታሪክ ሕግ አለና ! 

« ወፌ ቆመች » . . . ላንተ ቀለም 

የሕልም እንጀራ ከንቱ ሕመም 

« ትንሳኤ ሞት » . . . የሌለው ሞት 

ጸጋዬ ፤ ብዕርህ ይሙት 

               አልፎበታል . . . ይለፍበት 

               ጸጋዬ ሙት ! ይከተት ።


አሁን ነቢይ መኮንን የጨዋታ እንግዳ ላይ በድምፁ ወዳቀረበው እርግማኔን መልስልኝ ማለፍ እንችላለን። (ከ35 አመታት በኋላ የተፃፈ ነው) 


**** እርግማኔን መልስልኝ ― ከእሳቱ ተሰማ 1992 **** 


ከአቻምና በፊት አቻምና …

                የዛሬን አያድርገውና፤ 

ያኔ በልጅነቴ …

በአፍላ ደሜ፣ በፍላቴ፤ 

አለድግ አለመቀነት… እየሮጥኩ የታጠቁት፣ 

                ይጠልፍና ይጥለኛል …

አለልክ አለስፍሮቴ … እያወጋሁ የጎረስኩት፣ 

                 ማንቁርቴ ላይ ይጣበቃል …

… ብዬ በማልሸበር በማልዳዳበት ሰዓት፣  

በየካቲት ዋናተኞች … በዘራፊዎቹ …

               ተከብቤ በነበር ወቅት፤ 

                ሳላቅማማ ሳልገደር፣ 

ጸጋዬ ብዕርህ “ይሙት” … ብዬ ረግሜህ ነበር፣ 

                 … ወይ ጣጣዬ … የእኔ ነገር! 

ጸጋዬ በሥነ-ጥበብ፣ በሥነ-ግጥም ዓለም፤ 

                ምሰለኝ እንጂ … አልመስልህም 

                እወቀኝ እንጂ … አላውቅህም … 

                ይሄ ይውደም፣ ያ ይለምልም … 

 … ብሎ ፈሊጥ ነውር አይደለም? 

                አሳምረህ ታውቀዋለህ 

                ይቅር በለኝ፣ አልነግርህም፡፡ 

“… የቃለ ልሣን ቅመሙ 

                የባለቅኔ ቀለሙ 

                ነጠበ እንጂ ፈሰሰ አንበል፣ ቢዘነበል እንኳ ደሙ 

                ሰከነ እንጂ ከሰለ አንበል፣ ቢከሰከስ እንኳን አፅሙ… 

 … የቃለ እሳት ነበልባሉ 

                የድምፀ ብርሃን ፀዳሉ 

                የኅብረ ቀለማት ኃይሉ 

                አልባከነምና ውሉ 

                የዘር ንድፉ የፊደሉ 

                ቢሞት እንኳ ሞተ አትበሉ” 

ከሰው በፊት ያልከው አንተ፣ 

አቦ ተወኝ! … ተለመነኝ፤ 

አይን ለአይን አንተያይ፣ እርግማኔን መልስልኝ … 

                ለሀ… ሁህ፣ 

                ለአቡጊዳህ …

ለአዋሽ-ሰገዱ ዱታህ፤  

ምሰለኝህን እምቢ ብል፣ ብከፋብህ… ባመርብህ፣ 

                በበልግህ…

                በእሾህ አክሊልህ…

                በኦቴሎህ… በማክቤዝህ፣ 

                ጸጋዬ በአበባ እሳትህ… 

                የለም፣ በእሳት አበባህ… 

… እማረክ እማለላለሁ፤ 

በሥነ-ግጥም ጥማቴ…

የጸጋዬ ቤት ቤቴ፣… በሆነ እያልኩ እመኛለሁ! 

ብዕርህን ላይ ነው እምጓጓው፤ 

ልጠጋህ ነው እምንፏቀቀው፤ 

የቃላት ኅብረ ቀለምህን 

የሕይወት ስንክሳርህን … ጸጋዬ፣ የጸጋ ዳስክን 

              ፊደል አጣጣልህን 

               ድምፅ አወራረድህን 

               የቲያትር የምርምር የፈጠራ ተውህቦህን 

               እንደ ማክማክሳ ሙርቲ፣ 

               እንደ አምባሰል… እንደ ባቲ.. 

               እንደ በገና እሮሮ 

               እንደ ሙሾ እንጉርጉሮ …

 … እንደ ሰንጎ መገን ጉም 

                እንደ የወል ቤት እመም ....

 … እንደ ዳዊት ቀያይ ቤቶች

                እንደ ያሬድ ዝማሬዎች… 

ወርሰን የምናወርሰው 

ዘግነን እምንለግሰው…

የጸጋዬ የብዕር ልጅ፣ የጸጋዬ የግጥም ምት፤ 

ይደግ ይመንደግ እንጂ፣ እንዴት ይባላል ይሙት?! 

                ምን ቆርጦኝ ነው እንዲያ ያልኩት? 

ወንድሜ… ነውሬን ተውልኝ፤ 

               እባክህ ተባረክልኝ … 

               እግዜር ይስጤን ውሰድና…

               እርግማኔን መልስልኝ፡፡ 

ከእንግዲህ እኔ በምንም… 

ምሰለኝ እንጂ… አልመስልህም 

እወቀኝ እንጂ… አላውቅህም… 

                ምንም ቢሆን፣ አልልህም፡፡ 

ጽጌሬዳ ቀለሟ ቀይ፣ ብቻ ነው ብሎ ዘበት 

ያንተ ጎዳና ወደ ሲኦል፣ የእኔይቱ ወደ ገነት፤ … 

                 … ብሎ ፍጥም፣ ዝግት ግርግም፣ 

                 ፍካሬ-እቡይ ዛሬ የለም፡፡ … 

                 ጠብ ያለሽ በዳቦን አልፈን 

ተቸንፈን… አሸንፈን፤ አቸንፈን… ተሸንፈን …

                  አቦ ተወኝ! እባክህን፤…

ባንኳኳን ልንኳኳን መከራ ነው የመከረን፡፡


ነቢይ ግጥሙን አንብቦ ከጨረሰ በኋላ ከመዓዚ ጋር የተጨዋወቱትን መዝለል ቅር ስለሚያሰኝ እግረመንገድ እናንሳው። 


መዓዚ:- 

<<አብዮተኛ በነበረበት ጊዜ፣ በወጣትነት ትኩሳቱ ብዕርህ ይሙት አለው። በሰከነበት ጊዜ ደግሞ እርግማኔን መልስልኝ አለው። እኛ አገር የምናጣው ይሄ የመስለኛል ነብይ። በ20 አመት የሰራነውን ስራ በሀምሳ አመታችንም በስልሳም ድርቅ ብሎ ልክ ነው ማለት፤ critically ሚዛን ላይ አውጥቶ ለማየትም በር አለመክፈት ....እንደዛ አይነት ችግር አለ።>> 


ነብይ፡- 

<<ይኸውልሽ መዓዚ አሁን ይህን ግጥም ያነበቡ አንዳድን ወዳጆቼ፤ ...እንዳልሽው እኛው እሳት እራት የሚባለው ትውልድ ውስጥ የሚቆጠሩት የ60ዎቹ ሰዎች ውስጥ፣ "እንዴት በጋራ ጸጋዬን ኮንነነው ስናበቃ፤ እሺ ብለን በየመድረኩ በየቀበሌው ስናነብ ቆይተን ያንን ጸጋዬ ይሙት የሚል ግጥም፣ እንዴት ብቻውን ክዶን ይቅርታ ይጠይቃል" ብለው ተከራከሩኝ። በጣም ብዙ ሙግት ተሟገትን። ያልሽው element የመጉደሉ ጉዳይ ይሄ ነው አየሽ? ዛሬም ውስጣችን የመረረ ሰዎች አለን። ሰክነንም መጣፈጥ አልቻልንም... unfortunately! እና ይሄን አለመታደል እንዴት እንደምናሳካው እና እንደምንመልሰው ወደ ቦታው ................... ቦታውን የሳተ ብዙ ነገር ያለ መስሎ ይሰማኛል። ሂደቱ ረዥም ነው። 40 አመት ቀላል አይደለም ለእኛ እድሜ እንኳን። በዚህ ሂደት ውስጥ ስንት ዝግዛግ፣ ስንት ጠመዝማዛ፣ ስንት ሰርጥ፣ ስንት ጉድጓድ ውስጥ አልፈናል። ያንን ቦታ ቦታው አልመለስንም ................... ለዚህ አንዱ ጥሩ ምሳሌ ይሄ ነው እላለሁ። እርግማኔን መልስልኝ ማለት........>> 


ነብይ መኮንን ከመዓዛ ብሩ ጋር አድርገውት ከነበረ የቅዳሜ ጨዋታ ሶስተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ክፍል የተወሰደ። 


ሌላው ነቢይ እዚህ ጨዋታቸው ላይ ስለ በወረቀት መነጋገር ያነሳው ሃሳብ አለ። ሃሳቡን እዚህ እንደወረደ ማምጣቱ ተገቢ ስለሆነ ቀጥዬ ላካተው። 


<<ደስ የሚለኝ እዚህ ጋ ምኑ መሰለሽ? በወረቀት መነጋገር ጥሩ ነገር ነው። አንድ ያ ባህል ምናልባት አሁን ተጀምሮ እንደሆነ እኔ እንጃ። እንጂ በመሀል እንዳልነበረ አውቃለሁ። ለሁሉም ነገር ብዕር ከማንሳት ጦር ማንሳት ይቀላል። ከመወያየት መሰዳደብ፣ መተራረብ ይቀድማል። እና ይሄንን አካሄድ ያኔ እንደተጀመረው ብንቀጥለው ኖሮ እያልኩ በቁጭትም ጭምር ነው የምደሰተው። ምክንያቱም ለተጻፈ ነገር በተጻፈ ምላሽ ከጻፍሽ፣ ሀሳብ ነው ያፋጨሽው ሀሳብ ነው ያነጋገርሽው። ስለዚህ ያ ትልቅ ጅምር ነው ብዬ የምገምተው ዘመን ነበረ። በኋላም በጎህ፣ በአብዮታችን ኢትዮጵያ፣ እንደዚህ እንደዚህ እንዳየናቸው። ለእያንዳንዱ አርቲክል ሌላ መልስ እየተጻፈለት፣ ያ ሂደት ቀጥሎ ቢሆን ኖሮ እላለሁ ብዙ ጊዜ። በጣም ብዙ ነገር ያቃልልልን ነበር።>> 


በመጨረሻም አንድ ሂሳብ እንስራና ጽሑፌን ላጠናቅ። 'ፎርሳ ብላሽ'ን የጻፈው ሌላ ሰው ነው የሚል መረጃ እስካልመጣ ድረስ... የቱሉ ፎርሳ ደራሲ ከ17 አመት በኋላ፣ እሳቱ ተሰማም ከ35 አመት በኋላም መፃፋቸውን ልብ በሉ ለመንገድ!!!! ስለዚህ ሁለቱም በህይወት ለተጠቀሰው ጊዜ ነበሩ ማለት ነው። በኮሎኔል ፈቃደ ገብረየስ መጽሐፍ ላይ ደግሞ፣ በእርግጠኝነት ታረቀኝ በዳሣ ባድመ ጦርነት ጊዜ ድረስ ነበር..... ከዛም በኋላ አመቱ ባይገለፅም ለተወሰኑ ዓመታት በህይወት ነበር። በመጽሐፉ መሰረት የቀብሩ ጊዜ በ90ዎቹ ውስጥ ይመስላል። በዚህ መሰረት ከሄድን እሳቱ ተሰማ ግጥሙን ሲፅፍ ታረቀኝ በዳሣም በህይወት ነበር ማለት ነው። ይሄን ጠቃሚ መረጃ እንደያዝን እሳቱ ተሰማ ማን እንደነበር ብቻ ተባበሩኝ እያልኩ ነው ጽሑፌን የምጠቀልለው። ከዛ ሌላውን ሂሳብ እንደ አዲስ እንሰራዋለን። 


ነሐሴ 2018 ዓ.ም. 

እሪዮት አለሙ በላይ 

 Eriyot Alemu belay

ስለ ጸሐፊው/ዋ እርሶ የሚያውቁት የተለየ ነገር ካለ፣ እዚህ ሲጠቀስ የጎደለ ነገር ከተሰማዎት፣ አዲስ ተጨማሪ ስራ ሲያገኙም ኮመንት መስጫው እርሶን እየጠበቀ ነው።

Comment

Ads

advert
advert