የአዘጋጁ ማስታወሻ!!!


እንደ መነሻ


ጸሐፊዎቻችንን አንድ ቦታ የመሰብሰብ ፍላጎቴ የቆየ ነው። እንደ መነሻም ምክንያቶች ነበሩኝ። ኢትዮጵያ ውስጥ ለእውነት የተቃረቡ (ሁሉንም ማወቅ ስለማይቻል) ምን ያህል ጸሓፍት ተነስተዋል? በብዛት በምን በምን ርዕስ ላይ ያተኩሩ ነበር? የትኛው ዘመን ላይ እንዴት፣ ስለምን ያስቡ ነበር? አሁን ያሉት ከበፊቶቹስ በምን ይለያሉ? የመሳሰሉት ጥያቄዎች ራሴም ሳስባቸው ብቻ ደስ ስለሚሉኝና ከመጻሕፍት ጋርም ብዙ ስለምውል ቢያንስ እንደ መነሻ ዝርዝራቸው ይኑረኝ ብዬ አስብ ነበር። እየቆየ ሲሄድ ግን ሌላም ምክንያቶች እየተጨመሩልኝ መጡ። 


እንደምታውቁት አሁን ባለንበት ዲጂታል በሆነ ዓለም የኛን የሆኑ ጸሐፊዎቻችንን ስራ እንደልብ አለማግኘት ቅር የሚያሰኝ ነገር ነው። የሩቁን አይደለም የትላንት (አረ እንደውም የዛሬን) የአንድ ደራሲን ስራ  መረጃ እንደልብ ማግኘት ፈታኝ ነው። የውጪ መጽሐፍት (ምናልባት እንግሊዝኛ ዓለም አቀፍ ቋንቋ መሆኑን ግምት ውስጥ ብንከት እንኳ) በሌላ ቋንቋ የተጻፉ መጽሐፍትን መረጃ ማግኘት ግን  ያን ያህል አድካሚ አይደለም። ይሄን ችግር የሆነ ቦታ ላይ የሆነ ሰው ሊያስተካክለው ይገባል ብዬ አምን ነበር። 


መረጃ መፈለግ የሚለውን በደንብ እንየው። ለምሳሌ አበበ የተባለ ጸሐፊ "አበቢቱ" የሚል መጽሐፍ ጽፏል። የመጀመሪያው ነገር ዲጂታሉ ዓለም አበበንም አበቢቱንም አያውቃቸውም። ይሄ በራሱ አበቢቱን ላነበበ ሰው ችግር ላይኖረው ይችላል። ምክንያቱም አበቢቱን በአካል ያውቀዋልና። ግን አበቢቱን አንብቦ የተደሰተ ሰው የጸሐፊውን የአበበን ሌላ ስራ ማግኘት ይፈልጋል ብዬ አስባለሁ። ይሄን መረጃ አለማግኘት ከመጀመሪያው በከፋ ሁኔታ ያበሳጨዋል። ላይብረሪ ሄዶ በአቦሰጥ ሲፈለግ አስቡት ይሰቀጥጣል። አበበ ሌላ ስራ ባይኖረውስ? የአበበን ስራ የወደደ ግን መቆሚያው ማረጋገጡ ብቻ ነው። ይሄንንም ችግር የሆነ ቦታ ላይ የሆነ ሰው ሊቀርፈው ይገባል ብዬ አስብ ነበር። 


በሀገራችን እንደሚታወቀው ሥነ ጽሑፍ ሲባል ሁልጊዜ ፊለፊት የሚመጡ ሰዎች አሉ። በርግጥ ከመሬት ተነስተው ፊለፊት ሊመጡ እንዳልቻሉ አምናለሁ። ስራቸው ነው ፊለፊት ያመጣቸው። ሆኖም በብዙ ዓመታት ውስጥም ያ ድግግሞሽ አለመለወጡ ይሰለቻል። ይህ ሌሎችን መጋረድም መስሎ ይሰማኛል። ስለዚህ ምንም ፃፉ ምንም ግርዶሻቸውን መግለጥ ፊለፊት ለሚወጡ ሰዎች መንገድ መጥረግም ይሆናል ብዬ አስባለሁ። ሰው የሚያነባቸው፣ ሊያነባቸው የሚወጣም እንዳሉ ሲያውቃቸው ብቻ ነው። እናም ለሰው እንደምርጫው መጽሐፉን እና ጸሐፊውን ማስተዋወቁ ለአንባቢው ተነሳሽነትን ይፈጥራል ብዬ አስባለሁ። በዚህ አጋጣሚ ጸሐፊውን ፊለፊት የሚያወጣው አንባቢ ነውና እድሉ ለብዙሃኑ ክፍት ይሆናል። ቢያንስ 'በዚ ርዕስም የፃፈ አለ?' ብሎ ማሰቡ ራሱ አንድ ደረጃ ከፍ ማለት ነው። 


እግረ መንገዴን ይሄን ላንሳው። የአንድ ደራሲ ቀደምት ታሪኩ ከሙሉ መጽሐፍ ስራው መጀመር አለበት ብዬ በፅኑ አምናለሁ። የደራሲው ታሪክ በደራሲነቱ እስከሆነ ድረስ የሚነሳው ቀደምት ታሪኩ መጽሐፍቱ ብቻ ናቸው። ደራሲው ከተወለደበት ቀን ይልቅ የመጀመሪያ መጽሐፉን ያሳተመበት አመት ታሪኩን ሙሉ ያረገዋል ባይ ነኝ። ሁሉ ነገር ከደራሲው ስራዎች በኋላ የሚመጡ ናቸው። ስለ ደራሲያን የሚጻፉ በዛ ያሉ መጽሐፍት ላይ ይሄን ክፍተት ስላየው ነው። "አበበ ከ20 በላይ መጽሐፍ ጽፏል" ብሎ መዝጋት ታሪኩን ጎዶሎ ያረገዋል። ታሪክ ከሆነ ሃያው መጽሐፍት እነዚህ እነዚህ ናቸው ተብለው መገለፅ አለባቻው። እንዲህ ዓይነት አገላለፅ ሰዎችን ለጥርጣሬ ይጋብዛል። አንድ አንባቢ 'እውነት አበበ ከ20 በላይ መጽሐፍት ጽፏል?' ብሎ ቢጠይቅ አጠፋህ ልንለው የምንችል አይመስለኝም። ዘርዝረን መጻፍ ስንጀምር ነገሮች እየጠሩ ይመጣሉ። ከላይ ያለው አጭር አገላለፅ ለሶሻል ሚዲያ ጽሑፍ ግብአት ቢሆን ችግር የለውም። ታሪክ ከሆነ ግን ክፍተት ፈጣሪ መሆኑን እዚህ ጋር ተናግሬ ማለፍ ስላለብኝ ነው ያነሳሁት። 


በርግጥ ይሄ ችግር ያለው ጸሐፊውም ጋር ነው። ስለራሳቸው ስራ ሙሉ መረጃ ለመስጠት የሚቸገሩ ጸሐፊዎች እንዳሉ የገለፁ አንድ ሁለት ስለ ደራሲዎች የሚጽፉ ሰዎችም ገጥመውኛል። ደራሲያኑ ራሱ በመጽሐፎቻቸው ላይም ይሄ ችግር ይታያል። ለምሳሌ ሦስት መጽሐፍ ያለው ደራሲ ሦስተኛው መጽሐፉ ላይ ስለ ቀደሙት ሁለቱ ስራዎቹ በአግባቡ መጥቀስ አለበት። በቅደም ተከተላቸው ቢቻል ከነታተሙበት አመት ጋር። ይሄን ጥንቅቅ አርገው የሚጠቅሱ እንዳሉ ሁሉ ከነአካቴው የሚተዉት አያሌ ናቸው። አንዳንዶች ሰባተኛው ስራቸው ላይ ገልፀው አስረኛው ላይ ይዘሉታል። ወጥ ነገር የሌላቸው ብዙ አሉ። ተሳስቼ ካልሆነ ወይ ልብ ሳልለው ቀርቼ ይሄን የውጭ ሀገር መጽሐፍት ላይ ሲገጥመኝ አላስታውስም። 


በግል ስለ አንድ ደራሲ ቀድሜ ማወቅ የምፈልጋቸውን ሦስት ነገሮችን ላንሳ። ሌላው ታሪኩ ሁሉ ቀጥሎ የምፈልገው ጉዳይ ነው። 

1. ጸሐፊው ምን ይመስላል? ፎቶው!!!! ጸሐፊው ራሱ ፎቶውን መደበቅ የሚፈልግበት ጊዜ ቢኖርም እንኳ ያ ጊዜ ካለፈ በኋላ ግን ፎቶው እንዲታይለት ይፈልጋል ብዬ እንዳምን ያስገደዱኝ ብዙ ሰዎች አሉ። ለተቀረው አብዛኛው ጸሐፊ ግን ፎቶው ከስራው ጋር ተቆራኝቶ እንዲታይለት መፈለጉ ከመጽሐፍ ጀርባም ሆነ ፊለፊት የሚወጡ ፎቶዎች ምስክር ናቸው። እንደ እኔ ሳወራ ግን ደራሲውን በፎቶ ማየት ለተለያየ ምክንያት እፈልገዋለሁና ለኔ እጅግ መሰረታዊ ነገር ነው። 

2. ጸሐፊው ስንት ስራ አለው?

3. የመጀመሪያ ስራውን መቼ ሰራው? የመጨረሻውንስ? በመሃል ስንት ዓመት አለ? 


እነዚህ ነገሮች ለኔ የአንድ ጸሐፊ መነሻ ሙሉ ታሪኮች ናቸው ብዬ አምናለሁ። ዌብሳይቱንም በዚህ መንፈስ ነው ያዘጋጀሁት። የራሴን መሰረታዊ ፍላጎቶች ሳሟላ ነው የሌላውንም ማሟላት የምችለው ብዬ በፅኑ ስለማምን ነው። ሰው የራሱን ጥያቄ ሲመልስ ነው እግረመንገዱን ለሰው የሚተርፈው። ይሄም እምነቴ ነው። ወደ ዝርዝር ጉዳዬች እንለፍ።  



ስለ ደራሲያን እና ስራዎቻቸው ከዚ በፊት የተፃፉ መጻሕፍት ምን ይላሉ?


1. በኢትዮጵያ የሚገኙ መጻሕፍት ቁጥር 1904

ኅሩይ ወልደ ሥላሴ


ብዙ ፈልጌ አስፈልጌ ያጣሁት መጽሐፍ ነው። መኖሩን ግን አረጋግጫለሁ። Reidulf Knut Molvaer - Black Lions የተሰኘ መጽሐፉ ላይ ስለ ኅሩይ መጻሕፍት ዝርዝር ሲያነሳ ይሄን መጽሐፍ የ318 መጻሕፍት ዝርዝር የያዘ ብሎ ያነሳዋል። ሀብታሙ ግርማ ደምሴም - የሥነ ጽሁፍ ሰዎች እና ሥራዎቻቸው የሚል መጽሐፉ ላይ ቁጥሩን 317 ቢለውም መጽሐፉን ያነሳዋል። የራሳቸው የኅሩይ ወልደ ሥላሴም በ1920 እና በ1963 በታተሙ ሁለት መጽሐፎቻቸው ውስጥ ይሄ መጽሐፍ ቀደምት ሥራዎቻቸውን በሚገልፀው ክፍል ላይ ተካቷል። በ1920 በታተመው ቀጥሎ በማነሳው መጽሐፍ ላይ "የመጻሕፍት ቁጥር" ተብሎ የተጠቀሰ ሲሆን በ1963ቱ የአራት ስራዎች ስብስብ ላይ ደግሞ "በኢትዮጵያ የሚገኙ የመጻሕፍት ቁጥር" ተብሎ ተጠቅሷል። ኅሩይ የመጻሕፈት ቁጥር ብለው የገለጹት ይሄንኑ በ1920 የታተመውን መጽሐፍ ቢሆንስ የሚል ተከራካሪ ቢመጣ... የመጽሐፉ መውጫ ላይ "የመጻሕፍትን ካታሎግ ሶስተኛ በማሳትምበት ጊዜ ተዘንግተው የቀሩትን ያንዳንድ መጻሕፍ ስም ሰብስቤና ጨምሬ ለማሳተም ተስፋ አደርጋለሁ" ማለታቸው ከዚህ በፊት መታተሙን አስረጅ ሆኖ እናገኘዋለን። 


2. በኢትዮጵያ የሚገኙ በግዕዝና ባማሪኛ የተጻፉ የመጻሕፍት ካታሎግ 1920

ኅሩይ ወልደ ሥላሴ


ኅሩይ በመቅድማቸው ላይ ስለ ካታሎግ አስፈላጊነት የጻፉትን ላጋራችሁ። 


ደግሞ በቀድሞ ዘመን ከብሉይና ከሐዲስ መጻሕፍት በቀር የኢትዮጵያ መጻሕፍት ሁሉ ካታሎግ አልነበራቸውም። ካታሎግ ማለት የመጻሕፍትንም ቢሆን የሌላውንም የማናቸውንም ዓይነት ዕቃ ቢሆን ስሙንና ቁጥሩን ዋጋውንም ለይቶ የሚያስታውቅ መጽሐፍ ማለት ነው፤ ካታሎግ የሌለው መጽሐፍና ዕቃ በጋን ውስጥ እንደተበራ መብራት ነው፤ በጋን ውስጥ የተበራ መብራት ለሰዎች ሊያበራ እንደማይችል ካታሎግም የሌለውን መጽሐፍ ሰው ፈልጎ ሊያገኘው አይችልምና ለሰው እውቀትን አይሰጥም። 

 

መጽሐፉ በዝርዝሩ የያዛቸው መጻሕፍት የሚከተሉት ናቸው። 

- 46 የብሉይ መጻሕፍት

- 6 ከ46ቱ የማየቆጠሩ የብሉይ መጻሕፍት

- 35 የሐዲስ መጻሕፍት

- 13 ለቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የሚፈለጉ መጻሕፍት

- 6 ለቤተ ክርስቲያን የሚፈለጉ የዜማ መጻሕፍት

- 4 የሊቃውንት መጻሕፍት

- 26 የመጻሕፍት ትርጓሜ

- 3 የመነኮሳት መጽሐፍ

- 26 ጠቅላላ የአዋልድ መጻሕፍት

- 103 የገድል መጻሕፍት

- 110 ልዩ ልዩ የአዋልድ መጻሕፍት

- 14 የቁጥር መጻሕፍት ባሕረ ሀሳብ

- 40 የታሪክ መጻሕፍት

- 20 የኅሩይ ወልደ ሥላሴ መጽሐፍት

- 8 የፕሮፌሶር አፈ ወርቅ ዘብሔረ ዘጌ መጻሕፍት (አፈወርቅ ገብረየሱስ)

- 8 የአለቃ ታዬ መጻሕፍት

- 5 የዊዘንበርግ መጻሕፍት

- 3 የተወልደ ብርሃን መጻሕፍት

- 4 የዶክቶር ፋይትሎዊች መጻሕፍት

- 3 የቄስ ኤርክሶን መጻሕፍት

- 24 የቋንቋ መማሪያ መጻሕፍት

ጥቅል ድምር 517 መጻሕፍት ነው።

እኔ ስደምረው 507 ነው የመጣልኝ። ምናልባት ወይ የድምር ስህተት ነው አልያም የተዘለሉ 10 መጻሕፍት ሊኖሩ ይችላሉ። ግን ዋናው ነጥብ እስከ 1920 ድረስ ያሉ መጽሐፎቻችን ምን ይመስሉ ነበር የሚለውን ማየት ነው። 


3. ስለ ኢትዮጵያ ደራሲያን (1936 የተጻፈ) ምናልባት 1961 የታተመ

ፕሮፌሰር ታምራት አማኑኤል


ይህ መጽሐፍ የተጻፈው በ1936 ዓ.ም. ነው። የታተመበት ግልፅ አይደለም። መቅድሙ በከበደ ደስታ የተጻፈው በ1961 ዓ.ም. ስለሆነ የታተመው በዛው ዓመት ሊሆን ይችላል ብዬ እገምታለሁ። ፕሮፌሰር ታምራት በዚች ትንሽ ገጽ በያዘች መጽሐፍ የጽሑፋችንን አመጣጥ ከጥንት ምክንያታዊ በሆነ መንገድ ይተነትናል። እጅግ ሊነበብ የሚገባው መጽሐፍ ነው ብዬ ከመግለፅ ውጪ የዚ ጽሑፍ ዓላማ ያ ስላልሆነ በዚ ልዝለለው። በሶስት ዘመናት በከፈላቸው የአማርኛ ጽሑፍ ዘመናት ውስጥ የሚያነሳቸው ጸሓፍት የሚከተሉት ናቸው። 

- አለቃ ዘነብ
- አለቃ ወልደማርያም
- አለቃ ዘወልድ
- አቶ ዐጽሜ
- አለቃ ታየ
- ፕሮፌሰር አፈወርቅ ገብየሱስ
- በጅሮንድ ተክለሐዋርያት
- ነጋድራስ ገብረሕይወት
- ብላቴን ጌታ ኅሩይ
- አለቃ ኪዳነወልድ ክፍሌ
- ወጣት ከበደ ሚካኤል

4. የኢትዮጵያ እትማት: እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ፲፱፻፷፮ ዓ.ም. ፤ እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ፲፱፻፸፬ ዓ.ም. የታተሙ መጻሕፍት ጥራዞች ዓመታዊ ጽሑፎችና በመጽሔት የወጡ ድርሰቶች  1966

ደግፌ ገብረጻድቅ እና መርጊያ ዲሮ


ይህ መጽሐፍ በርዕሱ እንደተመላከተው በ1966 ዓ.ም. የታተሙ መጽሐፍ ሆነ መጽሔት በአማርኛ ይሁን በእንግሊዝኛ የታተሙ ጽሑፎችን ጥንቅቅ አርጎ ያካተተ መጽሐፍ ነው። ያውም በየ ዘውጋቸው ከፋፍሎ። እያንዳንዱ መጽሐፍ ሙሉ መረጃው አለ። የታተመበት ቦታ፣ ማተሚያ ቤቱ፣ የታተመበት ዓመት፣ የገፁ ብዛት፣ ቁመት መጠኑ ሁሉም ተካቷል። 


5. BLACK LIONS: The Creative Lives of Modern Ethiopia's Literary Giants and Pioneers 1997 (1989)

Reidulf Knut Molvaer


ይህ መጽሐፍ የ32 ጸሐፊዎቻችንን ሥራ ከነ ታሪካቸው ይዟል። የኛ ያልሆነ ሰው (በኋላ የኛ ልንለው ብንችል እንኳ) የኛን ስራ ስለሰራልን በእጅጉ ልናመሰግነው ይገባል ብዬ አምናለሁ። በአካል ማግኘት የሚችለውን በአካል አግኝቶ የማይችለውን ብዙ መረጃ አገላብጦ እንደጻፈው ያስታውቃል። ራሱም መረጃውን ያገኘበትን በግልፅ ስለሚያስቀምጠው። ለብዙ ሰዎችም ጥናታዊና መሰል ስራ መነሻ መሆኑ ግልፅ ነው። ጥቂት የማይባሉ መጻሕፍት ላይ ስሙ ከማጠቀሻ መጻሕፍት ጋር ተያይዞ ሲነሳ አይቻለሁ።  እዚህ ከዘረዘርኳቸው መጻሐፍት ጭምር። በዚህም በስነጽሑፍ ስራዎቻችን ላይ ትልቅ አሻራ ያስቀመጠ ሰው ነው ማለት ይኖርብናል። ሆኖም ድካሙን ብረዳም ውለታውን ባረሳም ትንጥዬ የሚባሉ ክፍተቶች ግን ያየሁ ይመስለኛል። ራሱም እንደሚሰማው አምናለሁ። ለምሳሌ ስለ ኅሩይ ሲያነሳ "ስለ ኀሩይ ብዙ መረጃዎች ከኔ ጥናት በኋላ ቢወጡም ቀደምት ጥናቴን ማሳተሙ ዋጋ ያለው መስሎ ታይቶኛል" ብሏል። ልክም ነው ሰው እስከደረሰበት ያለውን መስጠት ትልቅነትም ነው። 


ለምሳሌ ኅሩይ የጻፉትን በተራ ቁጥር 2 የጠቀስኩትን በ1920 ዓ.ም. የታተመውን ስራቸውን ያየው አልመሰለኝም። ቢያየው ኖሮ ዝርዝር ስራቸው ላይ የሆኑ ጥቂት ክፍተቶች አላይበትም ነበር። ሌላም ቦታ ላይ መሰል ነገሮች ስላየሁ ነው። ይሄን የማነሳው በሱ ብቻ አይደለም። ሁሉም ሰው ከላይ እስከ ታች ክፍተት ስላለበት ነው። ኅሩይም ዝርዝር መጻሕፍታቸው ላይ "የዘለልኳቸውን በቀጣይ አካትታለሁ" ማለታቸው ክፍተት አለብኝ እንደ ማለት ነው።  ማንም ሙሉ አይዶለም ለማለት ነው። መልህክቱ እየተላለፈ ያለው ይሄን ለሚያነበው ነው። እንጂ ጸሐፊው እጅግ እጅግ አድካሚውን ስራ የተወጣልን ባለውለታችን ነው። ከባድ፣ አድካሚና ክፍተት የማይጠፋው ስራ መሆኑን ሰው እንዲረዳውም ነው። በኛ ሀገር የመረጃ አያዛዛችን ደካማ ባህል የፈጠረው ችግር እንደሆነ ይሰማኛል። 


5.1) ጥቋቁር አናብስት (?)2013

ቴዎድሮስ ሸዋንግዛው እና ኤፍሬም ጀማል አብዱ (የቁጥር 3 መጽሐፍ ትርጉም)


ይህ ከላይ የተሳው መጽሐፍ ትርጉም ስለሆነ ለተርጓሚዎቹ ምስጋና ብቻ ነው ያለኝ። ለብዙሃኑ መዳረስ ያለበትን ስራ በማድረስ አላፊነታቸውን ስለተወጡ ምስጋና ይድረሳቸው። ብዙ ሰውም እንደተቀመበት አውቃለሁም አምናለሁም። 


6. ኅብረ ኢትዮጵያ ቅፅ 1 1999 ቅፅ 2 2009 

ቴዎድሮስ በየነ 


መጽሐፉ ጀርባ ላይ እንዲህ የሚል ጽሑፍ አለ። "በአቀራረቡ ልዩ፣ በይዘቱ ሰፊ እና ለአጠቃቀም ምቹ የኾነ የመረጃ መጽሐፍ" .... ልከኛ የሆነ መጽሐፉን የሚገልፅ አገላለፅ ስለሆነ ነው እዚህ ያጋራሁት። የመጽሐፉ ዓላማ ሥነ ጽሑፍ ብቻ አይደለም። ታሪክ፣ ስፖርት፣ ሰዎቻችን፣ ቅርስ የመሳሰሉት ክፍሎች አሉት። ሆኖም ሥነ ጽሑፍ ባለው ክፍል ላይ እኔ እንደምፈልገው መንገድ መረጃ ያገኘሁበት ልከኛ መጽሐፍ ነው። 

የያዛቸውን ዝርዝሮች ቀጣዩን ይመስላሉ
- 74 በኢትዮጵያ ሥነ-ጽሑፍ ታሪክ ጉልህ ድርሻ ያላቸው ጥንታዊ የሃይማኖት፣ የዜማ፣ የዘመን አቆጣጠር፣ የሥርዓትና የታሪክ መጻሕፈት ዝርዝር በከፊል
- 48 የኢትዮጵያ ቀደምትና አንጋፋ ደራስያንና ድርሰቶቻቸው
- 9 ልሳነ ዋህድ መዛግብተ ቃላት [አማርኛ በአማርኛ የሆኑ መዛግብተ ቃላት]
- 5 አማርኛን ከሌሎች የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጋር ለማተራጎም የተዘጋጁ መዛግብተ ቃላት
- 14 አማርኛን ከውጭ ሃገር ቋንቋዎች ጋር ለማተራጎም የተዘጋጁ መዛግብተ ቃላት
- 4 በአገራችን ውስጥ የተዘጋጁ ባለ ሦስት ቋንቋዎች መዛግብተ ቃላት

7. ከ፲፻ እስከ ፳፻ ዓ.ም. ያሠርቱ ምእት የብርዕ ምርት ክፍል ፩ 1999

ብርሃነ መስቀል ደጀኔ እና ጌታሁን ሽብሩ


ይሄን መጽሐፍ በአካል አላየሁትም። እንዳለ ሰምቻለሁ ግን አላረጋገጥኩም። በፒዲኤፍ ነው ያለኝ። በእንደዚህ ዓይነት ስራ ከተሰሩ ስራዎች ሁሉ ይሄን ለመግለፅ ቃል የማጣለት ስራ ነው። ከመግቢያ እስከ መውጫው የሚጣል የሌለው። ጠንቃቆች ለጠንቃቆች የሰሩት ምርጥዬ ስራ ነው። በግል አንድ መጽሐፍ ከታተመበት ዓመት ውጪ ሲገለፅ ምቾት አይሰጠኝም። እዚህ እጅግ ብዙ መጻሕፍት የሚነሱበት ቦታ ላይ 99 ፐርሰንት መጻሕፍት የታተሙበት ዓመት አልተገለፀም። ትዝ ብሎኝ አያውቅም። ምክንያቱም ጸሐፊያኑ ከዛ በላይ መጽሐፎቻችንን በዘውግ ዘውግ መንፈሳዊ ሥጋዊ የቀረ የለም ጥንቅቅ አድርገው ሰድረዋቸዋል። አስተያየቶቻቸው ምርጫዎቻቸው በቃ ሁሉ ነገራቸው ገዝቶኛል።  

 

ዝርዝር ስራቸውን ለማንሳት ያህል። ከታች በቁጥር የተገፀው በርዕሱ ዙሪያ የፃፉ ሰዎች እንጂ የመጻሕፍቱ ብዛት አይደለም። መጻሕፍቱ ከዚህ እጅግ ብዙ ናቸው። 
- 57 መልክአ ገድልና ነገረ መለኮት 
- 19 አንድምታ ትርጓሜ
- 10 ትምህርት
- 110 ታሪክ
- 69 ቋንቋ
- 58 ግጥምና ቅኔ
- 33 ልቦለድ
- 48 ተውኔት
- 25 ቤሳና ዐጭር ልቦለድ
- 6 ወግ
- 14 ተረቶችና ቀልዶች
- 10 ሥነ-ልቡናና ሳይንስ
- 12 ሥነ-መንግሥትና ፑሊቲካ
- 29 ፍልስፍናዊ እሳቤ
- 13 ሴት ጸሓፍት
- 71 ትርጉም
- 11 በልሳነ-እንግልጣር የጻፉ
- 66 የኢትዮጵያ ጥናት
+++ እንደ አጭር ማስታወሻ:- አንድ ደራሲ ሶስት አራት አምስት ቦታዎች ላይ ሊደጋገም ይችላል። ብቻውን ታሪክ፣ልቦለድ፣ ትርጉም የመሳሰሉትን ሊሰራ ስለሚችል። ስለዚህ ቁልቁል ለመደመር አይመችም። 

8. ታሪካዊ መዝገበ-ሰብ ከጥንት እስከ ዛሬ 2000

ፋንታሁን እንግዳ


ይህ መጽሐፍ ስለ ነገሥታት (መሪዎች)፣ አርበኞች፣ ሊቃውንት፣ ፖለቲከኞች፣ ኪነ-ጠቢባን፣ እስፖርተኞች እና ለሎች አጫጭር ታሪኮች የሚዳስስ ነው። እና ኪነ-ጠቢባን በሚለው ስር ስለ ተወሰኑ ጸሐፊያን ስለሚያነሳ ነው ዝርዝር ውስጥ ያካተትኩት። በተጨማሪም ከኪነ ጥበብ ሙያ ውጪ በሌላ ሙያ ላይ ያሉ ሰዎች መጽሐፍ ጽፈው ከሆነ በታሪኩ ላይ ስለሚያነሳው ነው። 


9. ያልተዘመረላቸው ቅፅ 1 እና 2 2005

ፍፁም ወልደማርያም


ፍፁም ያልተዘመረላቸው ሰዎችን በሚያነሳበት ቅፅ አንድ መጽሐፉ ላይ የ21 ሰዎችን ታሪክ ይዳስሳል። ከነዚህ ውስጥ በዛ ያሉት ጸሐፊያን ስለሆኑም ጭምር ነው ዝርዝሩ ውስጥ የተካተተው። ቅፅ ሁለትም የ20 ሰዎችን ታሪክ ይዳስሳል። በተመሳሳይ ሁኔታም በዚም መጽሐፍ በብዛት የተነሱት ጸሐፊያን ናቸው። 


10. ማዕቀብ 2006

እንዳለጌታ ከበደ


እንዳለጌታ እዚህ መጽሐፍ ላይ ድርሳነ ሳንሱር፣ መዋዕለ ደራስያን እና ነገረ መጻሕፍት ብሎ በከፈላቸው ሶስት ክፍሎች የሚነሱት ነገሮች በሙሉ ስለ መጻሕፍት እና ጸሐፊያን ስለሆነ ነው እዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተተው። አንዳንድ እሱ ያነሳቸው የጸሐፊያን ታሪኮች የሚገኙት እሱ ጋር ብቻ ናቸው። 


11. የሥነ ጽሁፍ ሰዎች እና ሥራዎቻቸው: ልቦለድ፣ የተውኔት ድርሠት እና ጋዜጠኝነት በኢትዮጵያ (ከ1850-1960ዎቹ) 2011

ሀብታሙ ግርማ ደምሴ


ሀብታሙ ይህን መጽሐፍ በሁለት ክፍሎች ነው የከፈለው። አንደኛው 'ሥነ ጽሁፍ በኢትዮጵያ' የሚለውን ሲዳስስ ክፍል ሁለቱ ደግሞ 'ታላላቅ ኢትዮጵያዊያን የስነ ጽሁፍ ሰዎች አጭጭር የህይወት ታሪክ' የሚለውን ይዟል። በሁለተኛው ክፍል ላይ የ19 ጸሐፊያን ታሪክ ይዳሰሳል። 


13. ማኅደረ ደራስያን ቅጽ ፩ 2011

ኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር


ይህ መጽሐፍ የ35 ደራስያንን ታሪክ የያዘ መጽሐፍ ነው። እዚህ መጽሐፍ ላይ ታሪካቸው የተካተቱት ሰዎች አዘጋጆቹ ባወጡት መስፈርት መሰረት መስፈርቱን የሚያሟሉ ጸሐፊያን ናቸው። ቀጣይ ቅጾችም የሚኖሩት ይመስል ነበር። ግን እስካሁን ባለኝ መረጃ ሌላ የወጣ አልመሰለኝም። 


14. የኢትዮጵያ ደራሲያንና ሥራዎቻቸው ክፍል አንድ 2011

ጌታቸው አበበ አየለ


ይህ የጋሽ ጌታቸው መጽሐፍ በዛ ያሉ ጸሐፊያን ታሪክ የተካተተበት መጽሐፍ ነው። በሁለት ምዕራፎች የተከፈለ ሲሆን የመጀመሪያው 'ከጥንት ደራሲዎቻችን' በሚለው ምዕራፉ የ7 ጸሐፊያንን ታሪክ ይዟል። በምዕራፍ ሁለት  'ከ1900 ጀምሮ ያሉ ደራስያን' በሚለው ደግሞ የ222 ደራስያንን ታሪክ ይዟል። በድምሩ 229 ጸሐፊያን ማለት ነው። ይህ እስካሁን ካየኋቸው እጅግ እጅግ ብዙው ነው። 

ጸጋዬ ገብረመድኅን ደብተራው

15. እኔ እዚህ ዌብሳይት ላይ ለመሰብሰብ የሞከርኩት


እስካሁን ስራውን በምዕራፍ በምዕራፍ ነው ስሰራው የነበረው። አሁን ባለሁበት ምዕራፍ ከድሮው ጀምሬ 2000 ዓ.ም. ላይ ደርሻለሁ። በዚህ ምዕራፍ የ1464 ጸሐፊያንን ስራ አካትቻለሁ (ለሁለት ለሁለት የተሰሩ ስራዎችን ጨምሮ)።  ብዛቱን አስቡትና ድካሙን ገምቱ። 2ሺ ላይ አየር ለመውሰድ ለምን ቆም እንዳልኩ እንዲገባቹ ነው። እስከ 2 ሺ ስል ግን እስከዛ ድረስ የጻፉ ሰዎችን እንጂ ስራቸው እስከዛሬም ድረስ ከተሻገረ ሙሉ ስራው ተካቷል። ለምሳሌ በ1999 ዓ.ም. አንድ መጽሐፍ የጻፈ ሰው ከ2ሺ በኋላ 20 ስራ ቢኖረው 20ውንም ስራ አካትቻለሁ። የቀሩኝ ከ2 ሺ በኋላ መጽሐፍ ማሳተም የጀመሩት ናቸው። ትንፋሽ ወስጄ በአንድ ዙር እሄድባቸዋለሁ። ከዚ በኋላ ያሉት አብዛኞቹ ጸሐፊያን ዲጂታል ዓለሙ ላይ ነዋሪ ስለሆኑ ደሞ እንተጋገዛለን ብዬ በሙሉ ልቤ አምናለሁ። 

የመረጃ ምንጮቼ የሚከተሉት ናቸው 
- ከላይ የተዘረዘሩት መጻሕፍት (እያንዳንዱን እያጣራው ለማረጋገጥ የቸረገረኝን እየዘለልኩ - ብዙ ክፍተቶች ስላየሁ)
- ለዓመታት የተጠራቀሙ በኋላ ኪሴ አጣጥፌ የማስቀምጣቸው ማስታወሻዎቼ  (ሕጋዊ ማስታወሻ ደብተር ይዞ መዞር ስለሚደብረኝ ነው - ምክንያቱን በውል አላውቀውም)
- ወመዘክር ላይብረሪ ከጫፍ እስከ ጫፍ ያሉ መጻሕፍት መደርደሪያዎች (እኔ በጎበኘኋቸው ጊዜ የወጡ አልያም የጠፉ መጻሕፍት ከሌሉ በቀር ሁሉንም መደርደሪያዎች አዳርሻለሁ። ሁሉንም አንቢባያለሁ ግን አላልኩም)
- አያሌ አሮጌ መጻሕፍት ቤቶች (በተወካይም በአካልም)
- ዲጂታል ዓለሙ ላይ በግልፅ የሚገኙ መረጃዎች

ክፍተቶቼ

- ከሁለት ሰው በላይ በጋራ የተሰሩ ስራዎችን አላካተትኩም። መጀመሪያ ዳታውን ለማስገባት አልመች ስላለኝ እየዘለልኩት ሄድኩና በመሃል በየግለሰቡ ስራ ላይ በጋራ የተሰሩ ስራዎች እያልኩ ለማስገባት ሞከርኩና መጀመሪያ የዘለልኳቸው ስለነበሩ እንዳለ መተዉን መረጥኩ። በጋራ የተሰሩ ስራዎች ያን ያህል ብዙ ስላልሆኑ በአንድ ዘውግ ትንሽ ጊዜ ወስጄ አስገባቸኋለሁ። 

- በተቋም ደረጃ የታተሙ ስራዎችንም አላካተትኩም። አንዳንድ ቦታዎች ላይ መጀመሪያ በተቋም ስም የተሰሩ ስራዎች፣ ለግለሰብ ስም ተሰጥተው ስላየው ማጣራት የሚፈልግ ጉዳይ ስላለበት ባጠቃላይ እንዲሁ ትቼው ነው። ይሄም ቁጥሩ ብዙ ስላልሆነ በቀጣይ የማስገባው ይሆናል። 

- ሃይማኖታዊ ስራዎች ላይ ክፍተት አለብኝ። ላይብረሪ ላገኛቸው ከምችላቸው መጻሕፍት በስተቀር ሌላ መነሻ ስለሌለኝ ስነሳ በዚህ ጉዳይ ክፍተት እንደሚኖርብኝ አምኜ ነው። እንዲ ስል ምንም መረጃ አላስገባሁም ማለት አይደለም። በሁሉም ቤተ እምነቶች ዙሪያ ብዙ ብዙ አስገብቻለሁ። ግን ሙሉ አይደለም። ክፍተቱን ብቻዬን ልሞላው አልችልም። እንደየ እምነታችሁ የተጻፉ መጽሐፎቻችሁን ብታጋሩኝ ነው ነገሩን ቀሊል የምናደርገው። ይሄም እንደሚሆን ባለ ሙሉ ተስፋ ነኝ። 

- ተውኔት ያልኳቸው ስራዎች ላይ ብዙዎቹን ማረጋገጥ አልቻልኩም። ተውኔት ያልኳቸውን ክፍሎች በሁለት ልክፈላቸው። አንደኛዎቹ አፃፃፋቸው ያንን የተከተሉት ናቸው።  እነዚህ በትክክል ራሴ ያየኋቸው እና የታተሙ ናቸው። ሁለተኛዎቹ በመድረክ የተመደረኩት ናቸው። እዚህ ጋር ነው ክፍተቴ። መድረክ ካገኙት ውስጥ የህትመት ብርሃን የሚያገኙት ጥቂቶች ናቸው። እነዚህ የታተሙት ለመረጃ ምንም ችግር የለባቸውም። የተቀሩትን ግን ከአንዳንድ መጻሕፍት ላይ ስለ ተውኔቱ የተጻፉ መረጃዎችን እንደ ወረደ የተቀበልኩት በእምነት ብቻ ነው። ላረጋግጥበት የምችልበት ምንም ዓይነት መንገድ አልነበረኝም። በነጠላ ተውኔት ላይ የሚሰሩ ሰዎች ካሉ ወደፊት ማጣራቱን ይሰሩልኛል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። 

ፍቶው ከመፅሃፍ ጀርባ

እዚህ ስራቸው ስለተካተቱ ጸሐፊያን አንዳንድ ነገሮች

1. ማዕረግ:- አለቃ፣ ሐጂ፣ አባ ከመሳሰሉት በቀር የጸሐፊያኑን የትኛውም ማዕረግ አልተጠቀምኩም። 
2.ሁሉንም አንተ ብዬ ነው የጠራሁት
ከላይ እንደገለፅኩት መረጃቸው የገባው የ1464 ሰዎች ናቸው። እነዚህን ሁሉ ሰዎች እሳቸው እሱ እያሉ መከፋፈሉ እጅግ አድካሚ ስራ ነው። ስለዚህ ሁሉም ወንዶች "ስራዎቹ" በሚል የተገለፁ ሲሆን የሴቶቹ ደግሞ "ስራዎቿ" ተብለው ተገልጸዋል። ይህ የሆነበት ምክንያት ድካም ለመቀነስ ስለሆነ አንድ ፎርማት ስለተዘጋጀ እንደሆነ ተረዱልኝ። እንጂ ለምድር ለሰማይ የከባበዱ ሰዎችን ጳጳሳትን ሼኾችን "ስራዎቹ" ብዬ አንተ የምል ሰው አይደለሁም። 'ጽሑፍ ስራ የምትሰራው ደግሞ የደራሲው ወጣት ነፍሱ ነች' ብለን ይሄን ነገር ተስማምተን እንለፈው። 

2. የህትመት ዓመት:- በተቻለኝ መጠን የአንድን መጽሐፍ የመጀመሪያውን እትመት ዓመት ለመጠቀም ሞክሬያለሁ። እኔ ካስገባሁት መረጃ የቀደመ ዓመት ከላችሁ ለማስተካከሉ ሁሌም ዝግጁ ነኝ። 

2. ስም አፃፃፍ አማርኛ እንግሊዝኛ እነ ኃይለ ማርያም ዓይነት ስሞች
4.1 እንግሊዝኛ ስም 
በተለየ አጋጣሚ ደራሲው ራሱ ስሙን በእንግሊዝኛ የሚፅበትን መንገድ ካየሁ ያንን ነው የወሰድኩት። በተለመደው Berhanu ደራሲው Brhanu ብሎ ከፃፈው ተቀዳሚ የማረገው የደራሲውን ነው። የደራሲውን ማግኘት ካልቻልኩ የተለመደውን አጻጻፍ ነው የተጠቀምኩት። 
4.2 አማርኛ ስም
በሚገርም ሁኔታ እጅግ አወዛጋቢ ሆኖ ማግኘቴ አስገርሞኛል። አንድ ደራሲ የተለያዩ መጽሐፎቹ ላይ የተለያየ የራሱን ስም አጻጻፍ አግኝቻለሁ። ለምሳሌ አንዱ ላይ ዓሊ ብሎ ያጻፈ ቀጣዩ ላይ አሊ ብሎ ሊጻፍ ይችላል ምሳሌ ነው። የባሰ የሚያስገርመው አንድ መጽሐፍ ሽፋን ገፁ ላይ ያለው የደራሲው ስምና በውስጥ ያለው መለያየቱ ነው። ውጪ ላይ ስዩም ተብሎ ውስጥ ሥዩም ሊሆን ይችላል ምሳሌ ነው።  አንድ ስምም ሦስት ዓይነት ሲፃፍ ገጥሞኛል። አምሃ፣ አምኃ፣ አምሐ ምሳሌ ነው። እና እንደዚህ አይነቱ ነገር ሲገጥመኝ የራሴን ምርጫ እወስዳለሁ። ይሄ ዌብሳይት ላይ ችግር ስላለው ነው የማነሳው ሥዩምን ስትፈልጉ በስዩም ልታገኙት አትችሉም። 'ኬዝ ሴንሴቲቭ' የሚለውን ያዙልኝ። 
3. ቀን እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር እንደ ፈረንጆች
አንድ ጸሐፊ ስራው ሁሉ የሀገር ውስጥ ቋንቋ ከሆነ የተጠቀምኩት ዓመተ ምህረትን ነው።
አንድ ጸሐፊ በእንግሊዝኛ ብቻ ቢጽፍ የተጠቀምኩት የውጪውን አቆጣጠር ብቻ ነው። 
በአማርኛም በእንግሊዝኛም ለጻፉ የተጠቀምኩት ብዛት ያላቸውን ስራ ነው። አማርኛው ከበዛ እንግሊዝኛውን በኛ አመት አደርገዋለሁ። በተቃራኒውም እንደዛው። 

አንድን ጸሐፊ ስንፈልግ እንዴት እናገኛለን

በአንድ ምሳሌ እንየው። የፈለግነው ስለ ሐዲስ አለማየሁ መረጃ ነው እንበል። SEARCH ማድረጊያው ቦታ ሄደን ሐዲስ አለማየሁ ብለን ብንፈልግ ቀጥታ ራሳቸው ይመጡልናል። በእንግሊዝኛም Haddis Alemayehu ብንል እንደዛው። ሐዲስ ብቻ ብለንም ሰርች ብናደርግ ካሉት ከሌሎች ሐዲሶች ጋር ያመጣልናል። አለማየሁ ብለን ብንጽፍም እንደዛው። ወይም በስራቸው መፈለግ እንችላለን። መጽሐፎቻቸው ላይ ባለው አፃፃፍ። ለምሳሌ 'ፍቅር እስከ መቃብር' ብለን ብንጽፍ ቀጥታ ሐዲስ ይመጡልናል። 'ፍቅር እሥከ መቃብር' ብንል ግን ስህተት ሰራን ማለት ነው። በሌሎችም ስራዎቻቸው እንደዚህ መፈለግ እንችላለን። ይህ ለሁሉም ጸሐፊያን ይሰራል። 


እንደ ወውጫ

እግዜር ረድቶኝ እስካሁን እነዚህን መረጃዎች አሰባስቢያለሁ። በእናንተ እርዳታ ደግሞ የጎደለ እየሞላችሁ፣ የተሳሳተ እያረማችሁ፣ አዲስ እየጨመራችሁ በጋራ መረጃችንን ሙሉ ማድረግ እንችላለን ብዬ በጽኑ አምናለሁ። እዚህ ላይ በሚገኙ አድራሻዎች በሙሉ ያገኙኛል። ለሚዳሰስ አድራሻ natidanhaile@gmail.com መገኛዬ ነው። ከዛሬ ጀምሮ ይህ ዌብሳይት የናንተም ጭምር ነው።


ብላቴን ጌታ ኅሩይ 98 ዓመት በሞላው መጽሐፋቸው ላይ "ማስታወቂያ" የምትል ገጽ አለቻቸው። ከፊሏን እኔ መውጫ ላረጋት ነው። እነኋት!!! 


ማስታወቂያ። 

ወዳጆቼ አንባቢዎች ሆይ። 

በኢትዮጵያ የሚገኙትን የመጻሕፍትን ካታሎግ መጻፋችን በሚቻለን ነገር ሁሉ ከመጻሕፍቱ አንዳንዱን እየፈለግን እንድናነብና እውቀትን እንድናገኝ ነው እንጂ ቁጥራቸውን ብቻ ለማወቅ አለመሆኑን ሁላችሁም ሳታውቁት አትቀሩምና  በትጋት እየፈለጋችሁ እንድታነቡ አሳስባችኋለሁ። 


አክባሪዮት እሪዮት አለሙ በላይ

Eriyot Alemu Belay

የኢትዮጵያ ጸሓፍት ዌብሳይት በውስጡ ምንም ዓይነት የመፅሃፍ ፒዲኤፍ ፋይል የለውም። አላማው ጸሓፊዎቹን እና ስራዎቻቸውን ብቻ መጥቀስ ነው።

Comment

Ads

advert
advert