እንደ መነሻ
ጸሐፊዎቻችንን አንድ ቦታ የመሰብሰብ ፍላጎቴ የቆየ ነው። እንደ መነሻም ምክንያቶች ነበሩኝ። ኢትዮጵያ ውስጥ ለእውነት የተቃረቡ (ሁሉንም ማወቅ ስለማይቻል) ምን ያህል ጸሓፍት ተነስተዋል? በብዛት በምን በምን ርዕስ ላይ ያተኩሩ ነበር? የትኛው ዘመን ላይ እንዴት፣ ስለምን ያስቡ ነበር? አሁን ያሉት ከበፊቶቹስ በምን ይለያሉ? የመሳሰሉት ጥያቄዎች ራሴም ሳስባቸው ብቻ ደስ ስለሚሉኝና ከመጻሕፍት ጋርም ብዙ ስለምውል ቢያንስ እንደ መነሻ ዝርዝራቸው ይኑረኝ ብዬ አስብ ነበር። እየቆየ ሲሄድ ግን ሌላም ምክንያቶች እየተጨመሩልኝ መጡ።
እንደምታውቁት አሁን ባለንበት ዲጂታል በሆነ ዓለም የኛን የሆኑ ጸሐፊዎቻችንን ስራ እንደልብ አለማግኘት ቅር የሚያሰኝ ነገር ነው። የሩቁን አይደለም የትላንት (አረ እንደውም የዛሬን) የአንድ ደራሲን ስራ መረጃ እንደልብ ማግኘት ፈታኝ ነው። የውጪ መጽሐፍት (ምናልባት እንግሊዝኛ ዓለም አቀፍ ቋንቋ መሆኑን ግምት ውስጥ ብንከት እንኳ) በሌላ ቋንቋ የተጻፉ መጽሐፍትን መረጃ ማግኘት ግን ያን ያህል አድካሚ አይደለም። ይሄን ችግር የሆነ ቦታ ላይ የሆነ ሰው ሊያስተካክለው ይገባል ብዬ አምን ነበር።
መረጃ መፈለግ የሚለውን በደንብ እንየው። ለምሳሌ አበበ የተባለ ጸሐፊ "አበቢቱ" የሚል መጽሐፍ ጽፏል። የመጀመሪያው ነገር ዲጂታሉ ዓለም አበበንም አበቢቱንም አያውቃቸውም። ይሄ በራሱ አበቢቱን ላነበበ ሰው ችግር ላይኖረው ይችላል። ምክንያቱም አበቢቱን በአካል ያውቀዋልና። ግን አበቢቱን አንብቦ የተደሰተ ሰው የጸሐፊውን የአበበን ሌላ ስራ ማግኘት ይፈልጋል ብዬ አስባለሁ። ይሄን መረጃ አለማግኘት ከመጀመሪያው በከፋ ሁኔታ ያበሳጨዋል። ላይብረሪ ሄዶ በአቦሰጥ ሲፈለግ አስቡት ይሰቀጥጣል። አበበ ሌላ ስራ ባይኖረውስ? የአበበን ስራ የወደደ ግን መቆሚያው ማረጋገጡ ብቻ ነው። ይሄንንም ችግር የሆነ ቦታ ላይ የሆነ ሰው ሊቀርፈው ይገባል ብዬ አስብ ነበር።
በሀገራችን እንደሚታወቀው ሥነ ጽሑፍ ሲባል ሁልጊዜ ፊለፊት የሚመጡ ሰዎች አሉ። በርግጥ ከመሬት ተነስተው ፊለፊት ሊመጡ እንዳልቻሉ አምናለሁ። ስራቸው ነው ፊለፊት ያመጣቸው። ሆኖም በብዙ ዓመታት ውስጥም ያ ድግግሞሽ አለመለወጡ ይሰለቻል። ይህ ሌሎችን መጋረድም መስሎ ይሰማኛል። ስለዚህ ምንም ፃፉ ምንም ግርዶሻቸውን መግለጥ ፊለፊት ለሚወጡ ሰዎች መንገድ መጥረግም ይሆናል ብዬ አስባለሁ። ሰው የሚያነባቸው፣ ሊያነባቸው የሚወጣም እንዳሉ ሲያውቃቸው ብቻ ነው። እናም ለሰው እንደምርጫው መጽሐፉን እና ጸሐፊውን ማስተዋወቁ ለአንባቢው ተነሳሽነትን ይፈጥራል ብዬ አስባለሁ። በዚህ አጋጣሚ ጸሐፊውን ፊለፊት የሚያወጣው አንባቢ ነውና እድሉ ለብዙሃኑ ክፍት ይሆናል። ቢያንስ 'በዚ ርዕስም የፃፈ አለ?' ብሎ ማሰቡ ራሱ አንድ ደረጃ ከፍ ማለት ነው።
እግረ መንገዴን ይሄን ላንሳው። የአንድ ደራሲ ቀደምት ታሪኩ ከሙሉ መጽሐፍ ስራው መጀመር አለበት ብዬ በፅኑ አምናለሁ። የደራሲው ታሪክ በደራሲነቱ እስከሆነ ድረስ የሚነሳው ቀደምት ታሪኩ መጽሐፍቱ ብቻ ናቸው። ደራሲው ከተወለደበት ቀን ይልቅ የመጀመሪያ መጽሐፉን ያሳተመበት አመት ታሪኩን ሙሉ ያረገዋል ባይ ነኝ። ሁሉ ነገር ከደራሲው ስራዎች በኋላ የሚመጡ ናቸው። ስለ ደራሲያን የሚጻፉ በዛ ያሉ መጽሐፍት ላይ ይሄን ክፍተት ስላየው ነው። "አበበ ከ20 በላይ መጽሐፍ ጽፏል" ብሎ መዝጋት ታሪኩን ጎዶሎ ያረገዋል። ታሪክ ከሆነ ሃያው መጽሐፍት እነዚህ እነዚህ ናቸው ተብለው መገለፅ አለባቻው። እንዲህ ዓይነት አገላለፅ ሰዎችን ለጥርጣሬ ይጋብዛል። አንድ አንባቢ 'እውነት አበበ ከ20 በላይ መጽሐፍት ጽፏል?' ብሎ ቢጠይቅ አጠፋህ ልንለው የምንችል አይመስለኝም። ዘርዝረን መጻፍ ስንጀምር ነገሮች እየጠሩ ይመጣሉ። ከላይ ያለው አጭር አገላለፅ ለሶሻል ሚዲያ ጽሑፍ ግብአት ቢሆን ችግር የለውም። ታሪክ ከሆነ ግን ክፍተት ፈጣሪ መሆኑን እዚህ ጋር ተናግሬ ማለፍ ስላለብኝ ነው ያነሳሁት።
በርግጥ ይሄ ችግር ያለው ጸሐፊውም ጋር ነው። ስለራሳቸው ስራ ሙሉ መረጃ ለመስጠት የሚቸገሩ ጸሐፊዎች እንዳሉ የገለፁ አንድ ሁለት ስለ ደራሲዎች የሚጽፉ ሰዎችም ገጥመውኛል። ደራሲያኑ ራሱ በመጽሐፎቻቸው ላይም ይሄ ችግር ይታያል። ለምሳሌ ሦስት መጽሐፍ ያለው ደራሲ ሦስተኛው መጽሐፉ ላይ ስለ ቀደሙት ሁለቱ ስራዎቹ በአግባቡ መጥቀስ አለበት። በቅደም ተከተላቸው ቢቻል ከነታተሙበት አመት ጋር። ይሄን ጥንቅቅ አርገው የሚጠቅሱ እንዳሉ ሁሉ ከነአካቴው የሚተዉት አያሌ ናቸው። አንዳንዶች ሰባተኛው ስራቸው ላይ ገልፀው አስረኛው ላይ ይዘሉታል። ወጥ ነገር የሌላቸው ብዙ አሉ። ተሳስቼ ካልሆነ ወይ ልብ ሳልለው ቀርቼ ይሄን የውጭ ሀገር መጽሐፍት ላይ ሲገጥመኝ አላስታውስም።
በግል ስለ አንድ ደራሲ ቀድሜ ማወቅ የምፈልጋቸውን ሦስት ነገሮችን ላንሳ። ሌላው ታሪኩ ሁሉ ቀጥሎ የምፈልገው ጉዳይ ነው።
1. ጸሐፊው ምን ይመስላል? ፎቶው!!!! ጸሐፊው ራሱ ፎቶውን መደበቅ የሚፈልግበት ጊዜ ቢኖርም እንኳ ያ ጊዜ ካለፈ በኋላ ግን ፎቶው እንዲታይለት ይፈልጋል ብዬ እንዳምን ያስገደዱኝ ብዙ ሰዎች አሉ። ለተቀረው አብዛኛው ጸሐፊ ግን ፎቶው ከስራው ጋር ተቆራኝቶ እንዲታይለት መፈለጉ ከመጽሐፍ ጀርባም ሆነ ፊለፊት የሚወጡ ፎቶዎች ምስክር ናቸው። እንደ እኔ ሳወራ ግን ደራሲውን በፎቶ ማየት ለተለያየ ምክንያት እፈልገዋለሁና ለኔ እጅግ መሰረታዊ ነገር ነው።
2. ጸሐፊው ስንት ስራ አለው?
3. የመጀመሪያ ስራውን መቼ ሰራው? የመጨረሻውንስ? በመሃል ስንት ዓመት አለ?
እነዚህ ነገሮች ለኔ የአንድ ጸሐፊ መነሻ ሙሉ ታሪኮች ናቸው ብዬ አምናለሁ። ዌብሳይቱንም በዚህ መንፈስ ነው ያዘጋጀሁት። የራሴን መሰረታዊ ፍላጎቶች ሳሟላ ነው የሌላውንም ማሟላት የምችለው ብዬ በፅኑ ስለማምን ነው። ሰው የራሱን ጥያቄ ሲመልስ ነው እግረመንገዱን ለሰው የሚተርፈው። ይሄም እምነቴ ነው። ወደ ዝርዝር ጉዳዬች እንለፍ።
ስለ ደራሲያን እና ስራዎቻቸው ከዚ በፊት የተፃፉ መጻሕፍት ምን ይላሉ?
1. በኢትዮጵያ የሚገኙ መጻሕፍት ቁጥር 1904
ኅሩይ ወልደ ሥላሴ
ብዙ ፈልጌ አስፈልጌ ያጣሁት መጽሐፍ ነው። መኖሩን ግን አረጋግጫለሁ። Reidulf Knut Molvaer - Black Lions የተሰኘ መጽሐፉ ላይ ስለ ኅሩይ መጻሕፍት ዝርዝር ሲያነሳ ይሄን መጽሐፍ የ318 መጻሕፍት ዝርዝር የያዘ ብሎ ያነሳዋል። ሀብታሙ ግርማ ደምሴም - የሥነ ጽሁፍ ሰዎች እና ሥራዎቻቸው የሚል መጽሐፉ ላይ ቁጥሩን 317 ቢለውም መጽሐፉን ያነሳዋል። የራሳቸው የኅሩይ ወልደ ሥላሴም በ1920 እና በ1963 በታተሙ ሁለት መጽሐፎቻቸው ውስጥ ይሄ መጽሐፍ ቀደምት ሥራዎቻቸውን በሚገልፀው ክፍል ላይ ተካቷል። በ1920 በታተመው ቀጥሎ በማነሳው መጽሐፍ ላይ "የመጻሕፍት ቁጥር" ተብሎ የተጠቀሰ ሲሆን በ1963ቱ የአራት ስራዎች ስብስብ ላይ ደግሞ "በኢትዮጵያ የሚገኙ የመጻሕፍት ቁጥር" ተብሎ ተጠቅሷል። ኅሩይ የመጻሕፈት ቁጥር ብለው የገለጹት ይሄንኑ በ1920 የታተመውን መጽሐፍ ቢሆንስ የሚል ተከራካሪ ቢመጣ... የመጽሐፉ መውጫ ላይ "የመጻሕፍትን ካታሎግ ሶስተኛ በማሳትምበት ጊዜ ተዘንግተው የቀሩትን ያንዳንድ መጻሕፍ ስም ሰብስቤና ጨምሬ ለማሳተም ተስፋ አደርጋለሁ" ማለታቸው ከዚህ በፊት መታተሙን አስረጅ ሆኖ እናገኘዋለን።
2. በኢትዮጵያ የሚገኙ በግዕዝና ባማሪኛ የተጻፉ የመጻሕፍት ካታሎግ 1920
ኅሩይ ወልደ ሥላሴ
ኅሩይ በመቅድማቸው ላይ ስለ ካታሎግ አስፈላጊነት የጻፉትን ላጋራችሁ።
ደግሞ በቀድሞ ዘመን ከብሉይና ከሐዲስ መጻሕፍት በቀር የኢትዮጵያ መጻሕፍት ሁሉ ካታሎግ አልነበራቸውም። ካታሎግ ማለት የመጻሕፍትንም ቢሆን የሌላውንም የማናቸውንም ዓይነት ዕቃ ቢሆን ስሙንና ቁጥሩን ዋጋውንም ለይቶ የሚያስታውቅ መጽሐፍ ማለት ነው፤ ካታሎግ የሌለው መጽሐፍና ዕቃ በጋን ውስጥ እንደተበራ መብራት ነው፤ በጋን ውስጥ የተበራ መብራት ለሰዎች ሊያበራ እንደማይችል ካታሎግም የሌለውን መጽሐፍ ሰው ፈልጎ ሊያገኘው አይችልምና ለሰው እውቀትን አይሰጥም።
መጽሐፉ በዝርዝሩ የያዛቸው መጻሕፍት የሚከተሉት ናቸው።
- 46 የብሉይ መጻሕፍት
- 6 ከ46ቱ የማየቆጠሩ የብሉይ መጻሕፍት
- 35 የሐዲስ መጻሕፍት
- 13 ለቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የሚፈለጉ መጻሕፍት
- 6 ለቤተ ክርስቲያን የሚፈለጉ የዜማ መጻሕፍት
- 4 የሊቃውንት መጻሕፍት
- 26 የመጻሕፍት ትርጓሜ
- 3 የመነኮሳት መጽሐፍ
- 26 ጠቅላላ የአዋልድ መጻሕፍት
- 103 የገድል መጻሕፍት
- 110 ልዩ ልዩ የአዋልድ መጻሕፍት
- 14 የቁጥር መጻሕፍት ባሕረ ሀሳብ
- 40 የታሪክ መጻሕፍት
- 20 የኅሩይ ወልደ ሥላሴ መጽሐፍት
- 8 የፕሮፌሶር አፈ ወርቅ ዘብሔረ ዘጌ መጻሕፍት (አፈወርቅ ገብረየሱስ)
- 8 የአለቃ ታዬ መጻሕፍት
- 5 የዊዘንበርግ መጻሕፍት
- 3 የተወልደ ብርሃን መጻሕፍት
- 4 የዶክቶር ፋይትሎዊች መጻሕፍት
- 3 የቄስ ኤርክሶን መጻሕፍት
- 24 የቋንቋ መማሪያ መጻሕፍት
ጥቅል ድምር 517 መጻሕፍት ነው።
እኔ ስደምረው 507 ነው የመጣልኝ። ምናልባት ወይ የድምር ስህተት ነው አልያም የተዘለሉ 10 መጻሕፍት ሊኖሩ ይችላሉ። ግን ዋናው ነጥብ እስከ 1920 ድረስ ያሉ መጽሐፎቻችን ምን ይመስሉ ነበር የሚለውን ማየት ነው።
3. ስለ ኢትዮጵያ ደራሲያን (1936 የተጻፈ) ምናልባት 1961 የታተመ
ፕሮፌሰር ታምራት አማኑኤል
ይህ መጽሐፍ የተጻፈው በ1936 ዓ.ም. ነው። የታተመበት ግልፅ አይደለም። መቅድሙ በከበደ ደስታ የተጻፈው በ1961 ዓ.ም. ስለሆነ የታተመው በዛው ዓመት ሊሆን ይችላል ብዬ እገምታለሁ። ፕሮፌሰር ታምራት በዚች ትንሽ ገጽ በያዘች መጽሐፍ የጽሑፋችንን አመጣጥ ከጥንት ምክንያታዊ በሆነ መንገድ ይተነትናል። እጅግ ሊነበብ የሚገባው መጽሐፍ ነው ብዬ ከመግለፅ ውጪ የዚ ጽሑፍ ዓላማ ያ ስላልሆነ በዚ ልዝለለው። በሶስት ዘመናት በከፈላቸው የአማርኛ ጽሑፍ ዘመናት ውስጥ የሚያነሳቸው ጸሓፍት የሚከተሉት ናቸው።
4. የኢትዮጵያ እትማት: እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ፲፱፻፷፮ ዓ.ም. ፤ እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ፲፱፻፸፬ ዓ.ም. የታተሙ መጻሕፍት ጥራዞች ዓመታዊ ጽሑፎችና በመጽሔት የወጡ ድርሰቶች 1966
ደግፌ ገብረጻድቅ እና መርጊያ ዲሮ
ይህ መጽሐፍ በርዕሱ እንደተመላከተው በ1966 ዓ.ም. የታተሙ መጽሐፍ ሆነ መጽሔት በአማርኛ ይሁን በእንግሊዝኛ የታተሙ ጽሑፎችን ጥንቅቅ አርጎ ያካተተ መጽሐፍ ነው። ያውም በየ ዘውጋቸው ከፋፍሎ። እያንዳንዱ መጽሐፍ ሙሉ መረጃው አለ። የታተመበት ቦታ፣ ማተሚያ ቤቱ፣ የታተመበት ዓመት፣ የገፁ ብዛት፣ ቁመት መጠኑ ሁሉም ተካቷል።
5. BLACK LIONS: The Creative Lives of Modern Ethiopia's Literary Giants and Pioneers 1997 (1989)
Reidulf Knut Molvaer
ለምሳሌ ኅሩይ የጻፉትን በተራ ቁጥር 2 የጠቀስኩትን በ1920 ዓ.ም. የታተመውን ስራቸውን ያየው አልመሰለኝም። ቢያየው ኖሮ ዝርዝር ስራቸው ላይ የሆኑ ጥቂት ክፍተቶች አላይበትም ነበር። ሌላም ቦታ ላይ መሰል ነገሮች ስላየሁ ነው። ይሄን የማነሳው በሱ ብቻ አይደለም። ሁሉም ሰው ከላይ እስከ ታች ክፍተት ስላለበት ነው። ኅሩይም ዝርዝር መጻሕፍታቸው ላይ "የዘለልኳቸውን በቀጣይ አካትታለሁ" ማለታቸው ክፍተት አለብኝ እንደ ማለት ነው። ማንም ሙሉ አይዶለም ለማለት ነው። መልህክቱ እየተላለፈ ያለው ይሄን ለሚያነበው ነው። እንጂ ጸሐፊው እጅግ እጅግ አድካሚውን ስራ የተወጣልን ባለውለታችን ነው። ከባድ፣ አድካሚና ክፍተት የማይጠፋው ስራ መሆኑን ሰው እንዲረዳውም ነው። በኛ ሀገር የመረጃ አያዛዛችን ደካማ ባህል የፈጠረው ችግር እንደሆነ ይሰማኛል።
5.1) ጥቋቁር አናብስት (?)2013
ቴዎድሮስ ሸዋንግዛው እና ኤፍሬም ጀማል አብዱ (የቁጥር 3 መጽሐፍ ትርጉም)
ይህ ከላይ የተሳው መጽሐፍ ትርጉም ስለሆነ ለተርጓሚዎቹ ምስጋና ብቻ ነው ያለኝ። ለብዙሃኑ መዳረስ ያለበትን ስራ በማድረስ አላፊነታቸውን ስለተወጡ ምስጋና ይድረሳቸው። ብዙ ሰውም እንደተቀመበት አውቃለሁም አምናለሁም።
6. ኅብረ ኢትዮጵያ ቅፅ 1 1999 ቅፅ 2 2009
ቴዎድሮስ በየነ
መጽሐፉ ጀርባ ላይ እንዲህ የሚል ጽሑፍ አለ። "በአቀራረቡ ልዩ፣ በይዘቱ ሰፊ እና ለአጠቃቀም ምቹ የኾነ የመረጃ መጽሐፍ" .... ልከኛ የሆነ መጽሐፉን የሚገልፅ አገላለፅ ስለሆነ ነው እዚህ ያጋራሁት። የመጽሐፉ ዓላማ ሥነ ጽሑፍ ብቻ አይደለም። ታሪክ፣ ስፖርት፣ ሰዎቻችን፣ ቅርስ የመሳሰሉት ክፍሎች አሉት። ሆኖም ሥነ ጽሑፍ ባለው ክፍል ላይ እኔ እንደምፈልገው መንገድ መረጃ ያገኘሁበት ልከኛ መጽሐፍ ነው።
7. ከ፲፻ እስከ ፳፻ ዓ.ም. ያሠርቱ ምእት የብርዕ ምርት ክፍል ፩ 1999
ብርሃነ መስቀል ደጀኔ እና ጌታሁን ሽብሩ
ይሄን መጽሐፍ በአካል አላየሁትም። እንዳለ ሰምቻለሁ ግን አላረጋገጥኩም። በፒዲኤፍ ነው ያለኝ። በእንደዚህ ዓይነት ስራ ከተሰሩ ስራዎች ሁሉ ይሄን ለመግለፅ ቃል የማጣለት ስራ ነው። ከመግቢያ እስከ መውጫው የሚጣል የሌለው። ጠንቃቆች ለጠንቃቆች የሰሩት ምርጥዬ ስራ ነው። በግል አንድ መጽሐፍ ከታተመበት ዓመት ውጪ ሲገለፅ ምቾት አይሰጠኝም። እዚህ እጅግ ብዙ መጻሕፍት የሚነሱበት ቦታ ላይ 99 ፐርሰንት መጻሕፍት የታተሙበት ዓመት አልተገለፀም። ትዝ ብሎኝ አያውቅም። ምክንያቱም ጸሐፊያኑ ከዛ በላይ መጽሐፎቻችንን በዘውግ ዘውግ መንፈሳዊ ሥጋዊ የቀረ የለም ጥንቅቅ አድርገው ሰድረዋቸዋል። አስተያየቶቻቸው ምርጫዎቻቸው በቃ ሁሉ ነገራቸው ገዝቶኛል።
8. ታሪካዊ መዝገበ-ሰብ ከጥንት እስከ ዛሬ 2000
ፋንታሁን እንግዳ
ይህ መጽሐፍ ስለ ነገሥታት (መሪዎች)፣ አርበኞች፣ ሊቃውንት፣ ፖለቲከኞች፣ ኪነ-ጠቢባን፣ እስፖርተኞች እና ለሎች አጫጭር ታሪኮች የሚዳስስ ነው። እና ኪነ-ጠቢባን በሚለው ስር ስለ ተወሰኑ ጸሐፊያን ስለሚያነሳ ነው ዝርዝር ውስጥ ያካተትኩት። በተጨማሪም ከኪነ ጥበብ ሙያ ውጪ በሌላ ሙያ ላይ ያሉ ሰዎች መጽሐፍ ጽፈው ከሆነ በታሪኩ ላይ ስለሚያነሳው ነው።
9. ያልተዘመረላቸው ቅፅ 1 እና 2 2005
ፍፁም ወልደማርያም
ፍፁም ያልተዘመረላቸው ሰዎችን በሚያነሳበት ቅፅ አንድ መጽሐፉ ላይ የ21 ሰዎችን ታሪክ ይዳስሳል። ከነዚህ ውስጥ በዛ ያሉት ጸሐፊያን ስለሆኑም ጭምር ነው ዝርዝሩ ውስጥ የተካተተው። ቅፅ ሁለትም የ20 ሰዎችን ታሪክ ይዳስሳል። በተመሳሳይ ሁኔታም በዚም መጽሐፍ በብዛት የተነሱት ጸሐፊያን ናቸው።
10. ማዕቀብ 2006
እንዳለጌታ ከበደ
እንዳለጌታ እዚህ መጽሐፍ ላይ ድርሳነ ሳንሱር፣ መዋዕለ ደራስያን እና ነገረ መጻሕፍት ብሎ በከፈላቸው ሶስት ክፍሎች የሚነሱት ነገሮች በሙሉ ስለ መጻሕፍት እና ጸሐፊያን ስለሆነ ነው እዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተተው። አንዳንድ እሱ ያነሳቸው የጸሐፊያን ታሪኮች የሚገኙት እሱ ጋር ብቻ ናቸው።
11. የሥነ ጽሁፍ ሰዎች እና ሥራዎቻቸው: ልቦለድ፣ የተውኔት ድርሠት እና ጋዜጠኝነት በኢትዮጵያ (ከ1850-1960ዎቹ) 2011
ሀብታሙ ግርማ ደምሴ
ሀብታሙ ይህን መጽሐፍ በሁለት ክፍሎች ነው የከፈለው። አንደኛው 'ሥነ ጽሁፍ በኢትዮጵያ' የሚለውን ሲዳስስ ክፍል ሁለቱ ደግሞ 'ታላላቅ ኢትዮጵያዊያን የስነ ጽሁፍ ሰዎች አጭጭር የህይወት ታሪክ' የሚለውን ይዟል። በሁለተኛው ክፍል ላይ የ19 ጸሐፊያን ታሪክ ይዳሰሳል።
13. ማኅደረ ደራስያን ቅጽ ፩ 2011
ኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር
ይህ መጽሐፍ የ35 ደራስያንን ታሪክ የያዘ መጽሐፍ ነው። እዚህ መጽሐፍ ላይ ታሪካቸው የተካተቱት ሰዎች አዘጋጆቹ ባወጡት መስፈርት መሰረት መስፈርቱን የሚያሟሉ ጸሐፊያን ናቸው። ቀጣይ ቅጾችም የሚኖሩት ይመስል ነበር። ግን እስካሁን ባለኝ መረጃ ሌላ የወጣ አልመሰለኝም።
14. የኢትዮጵያ ደራሲያንና ሥራዎቻቸው ክፍል አንድ 2011
ጌታቸው አበበ አየለ
15. እኔ እዚህ ዌብሳይት ላይ ለመሰብሰብ የሞከርኩት
ክፍተቶቼ
እዚህ ስራቸው ስለተካተቱ ጸሐፊያን አንዳንድ ነገሮች
አንድን ጸሐፊ ስንፈልግ እንዴት እናገኛለን
በአንድ ምሳሌ እንየው። የፈለግነው ስለ ሐዲስ አለማየሁ መረጃ ነው እንበል። SEARCH ማድረጊያው ቦታ ሄደን ሐዲስ አለማየሁ ብለን ብንፈልግ ቀጥታ ራሳቸው ይመጡልናል። በእንግሊዝኛም Haddis Alemayehu ብንል እንደዛው። ሐዲስ ብቻ ብለንም ሰርች ብናደርግ ካሉት ከሌሎች ሐዲሶች ጋር ያመጣልናል። አለማየሁ ብለን ብንጽፍም እንደዛው። ወይም በስራቸው መፈለግ እንችላለን። መጽሐፎቻቸው ላይ ባለው አፃፃፍ። ለምሳሌ 'ፍቅር እስከ መቃብር' ብለን ብንጽፍ ቀጥታ ሐዲስ ይመጡልናል። 'ፍቅር እሥከ መቃብር' ብንል ግን ስህተት ሰራን ማለት ነው። በሌሎችም ስራዎቻቸው እንደዚህ መፈለግ እንችላለን። ይህ ለሁሉም ጸሐፊያን ይሰራል።
እንደ ወውጫ
እግዜር ረድቶኝ እስካሁን እነዚህን መረጃዎች አሰባስቢያለሁ። በእናንተ እርዳታ ደግሞ የጎደለ እየሞላችሁ፣ የተሳሳተ እያረማችሁ፣ አዲስ እየጨመራችሁ በጋራ መረጃችንን ሙሉ ማድረግ እንችላለን ብዬ በጽኑ አምናለሁ። እዚህ ላይ በሚገኙ አድራሻዎች በሙሉ ያገኙኛል። ለሚዳሰስ አድራሻ natidanhaile@gmail.com መገኛዬ ነው። ከዛሬ ጀምሮ ይህ ዌብሳይት የናንተም ጭምር ነው።
ብላቴን ጌታ ኅሩይ 98 ዓመት በሞላው መጽሐፋቸው ላይ "ማስታወቂያ" የምትል ገጽ አለቻቸው። ከፊሏን እኔ መውጫ ላረጋት ነው። እነኋት!!!
ማስታወቂያ።
ወዳጆቼ አንባቢዎች ሆይ።
በኢትዮጵያ የሚገኙትን የመጻሕፍትን ካታሎግ መጻፋችን በሚቻለን ነገር ሁሉ ከመጻሕፍቱ አንዳንዱን እየፈለግን እንድናነብና እውቀትን እንድናገኝ ነው እንጂ ቁጥራቸውን ብቻ ለማወቅ አለመሆኑን ሁላችሁም ሳታውቁት አትቀሩምና በትጋት እየፈለጋችሁ እንድታነቡ አሳስባችኋለሁ።
አክባሪዮት እሪዮት አለሙ በላይ
Eriyot Alemu Belay














