ዲያሌክቲካዊና የታሪክ ቁስ አካልነት ሂስ አደፍርስ


✍️✍️✍️✍️✍️


ደራሲ - ኃይሌ ፊዳ

የመጽሐፉ ርዕስ - ዲያሌክቲካዊና የታሪክ ቁስ አካልነት

ሃያሲ  - አደፍርስ

ጽሑፉ የወጣበት ቦታ - ጎሕ መጽሔት

ዘመን - የካቲት እና መጋቢት 1968 ..


✍️✍️✍️✍️✍️


በአገራችን በመካሄድ ላይ ያለው ሕዝባዊ ንቅናቄ ትክክለኛ ግቡን ሊመታ የሚችለው በላብአደሩና በላብአደሩ ርዕዮተ ዓለም ሲመራ መሆኑን ካለው ተጨባጭ ሁናቴና ከሌሎች አገሮች ታሪክ ተረድተነዋል። የላብ አደሩንም ርዕዮተዓለም በትክክለኛ መልኩ ከአገራችን ተጨባጭ ሁናቴ ጋር በማገናዘብ በኢትዮጵያ ቋንቋዎች በማቅረብ የውጭ ቋንቋ ለማንበብና ለመረዳት የሚያዳግታቸውን ላብአደሮችና ጭቁን መደቦች በትዮሪው ማስታጠቅ እጅግ አስፈላጊ ነው። 


ከጥቂት ጊዜ ወዲህ አንዳአንድ «ማርክሳዊ»መጻሕፍት በአማርኛ ብቅ ብቅ ማለት ጀምረዋል። ከነዚህም ውስጥ አንዱ ከኃይሌ ፊዳ የተጻፈው ዲያሌክታካዊና የታሪክ ቁስ አካልነት የተባለው ነው። የማርክሳዊ ሌኒናዊ መሰረተ ፍልስፍናን ለማቅረብ ይሞክራል። መጽሐፉ ምንም እንኳ በአማርኛ ተሰናድቶ በመቅረብ ወደፊትም በሌሎች የኢትዮጵያ ቋንቋዎች መጻፍ አስፈላጊነቱን በመግለጹ ቢመሰገንም በውስጡ አይነተኛና መሰረታዊ የሆኑ ሥህተቶችን በመሥራቱ መተቸት አስፈላጊ ሆኖ አግኝቸዋለሁ። 


ምንም እንኳ የፍልስፍናውን መሰረተ ኃሳቦች ለማስቀመጥ ግልጽ የሆኑ ትርጉሞችን ቢሰጥም ለጊዜው ግልጽ ባልሆነ ምክንያት ኃሳባችን በመቆንጠብ ፤ አንድ ቦታ የሳተውን እንደገና በማስተካከል ፤ በትክክል ፤ የሰራውን እንደገና በማፍረስ ፤ ትርጉም የለሽ ምሳሌዎችን በመደንጎር ይዘቱ «ማስተማርና ማደናገር» እንዲሆን አድርጎታል። ጠቅላላ ይዘቱንም ከመተቸት ሥህተት የሆኑትን ክፍሎች በማውጣት መነጋገር አስፈላጊ በመሆኑ እንመልከታቸው። 


ገና ከመግቢያው ዋና መሰረታዊ የሆኑ ሥህተቶች እናገኛለን።«ፍልስፍና ሳይንስ ነው» ገጽ ፩። ይህ በጣም ድፍንና ትርጉም የለሽ አስተያየት በጣም የሚያምታታ ተራ አገላለጽ ነው። ሕሊናዊነት ሳይንስ ነው? የፕሌቶ ፍልስፍና ሳይንስ ነው?። መቸም የሳይንስንና የፍልስፍናን አንድነትና ውህደት ጠለቅ ብሎ መከራከሩ ለአሁኑ «ትችት» በጣም አስፈላጊ መስሎ ባይታይም በመጠኑ እንመልከተው። 


ከማርክሳዊነት አቋም አንጻር ፍልስፍና ማለት የሳይንስን ውጤቶች (ማስረጃዎች) ከታሪክ የተገኙ ልምዶችን በአንድ በተወሰነ የሕብረተሰብ ደረጃ የመደብ አቋም ጋር ተቀነባብሮ የንድፈ ሐሳብ መስተጻምሮ (ቲዩሬቲካል ሴንቲሲስ) ነው። በዚህ ምክንያትም ነው በአንድ የታሪክ እድገት ደረጃ ላይ ያሉ የሳይንስ ውጤቶች በተለያዩ የፍልስፍና ቡድኖች እንደተፈለጉ የሚተረጉሙት። ለምሳሌ የዳርዊንን ኦርጅን ኦፍ ስፔሽስን ማቴሪያሊስት ፈላስፋዎች የኃይማኖትን ተረት ሲሰብኩበት ሌሎቹ ደግሞ የከበርቴ ሊቃውንት በተለይ አድኃሪና ከሳይንስ የላቀ ትርጉም በመስጠት ሶሻል ዳሪዮን የሚል የፍልስፍና ማወናበድ ጀመሩበት። አንድን የሳይንስ ፍልስፍና በመውሰድ ሁሉም እንደ ፍልስፍናው (ቁስአካላዊ ወይም ሕሊናዊ አድርጎ) ይጠቀምበታል። ፍልስፍና እላይ እንደተባለው ሳይንሳዊ ማስረጃዎችን ከሕብረተሰቡ የታሪክ ማስረጃ ጋር አጣምሮና አዋህዶ አጠቃላይ የፍጥረትን ፤ የሕብረተሰብንና የአስተሳሰብ ትርጉም መስጠት ነው። ማርክሳዊ ፍልስፍና ከሌሎቹ ፍልስፍናዎ ችም የሚለየው ዘመናዊ ሳይንስን በትክክለኛ ትርጉም በመውሰድ በዲያሌክቲካዊ አመለካከት ታሪክን በትክክል የሚተረጉም ትክክለኛ «ሳይንሳዊ ፍልስፍና» በመሆኑ ነው። እንደ አቶ ኃይሌ አባባል ማንኛውንም ፍልስፍና «ሳይንስ» አድርጎ ማቅረብ ባጠቃላይ በሁለት ዋና ዋና ስህተቶች ላይ ይጥለናል ። አንደኛ ፤ ፍልስፍናን በሙሉ (ሁለቱን ፊናዎች ቁስአካላዊና ህሊናዊ) ሳይንሳዊ በማድረግ ሁለቱንም የፍልስፍና ፊናዎች እውነት ሊያሰኛቸው ነው። ሁለተኛ ፤ ፍልስፍና መሰረቱን ሳይንስ ብቻ በማስመሰል ሌሎቹን አብረው የሚሄዱትን በመካድ ያሳስታል ያወናብዳል። 


በዚሁ መግቢያ ላይ ገጽ ፪ በጣም አስቂኝ የሆኑ ሁለት ስህተቶች እንመለከታለን «የሕብረሰባዊነት ፍልስፍና ማርክሲዝም ሌኒንዝም ይባላል። ........ ይህ ፍልስፍና በታሪክ ከታዩት ፍልስፍናዎች ሁሉ ሳይንሳዊና የተሟላ ከመሆኑም በላይ ፤ የሰው ልጅ እውቀት ባደገ ቁጥር ከዚያ እየተመገበ ፤ እየዳበረ የሚሄድ ነው።» ምን ለማለት ነው? ሶሻሊዝም ከተባለ ሁሉም ማርክሳዊ ሌኒናዊ ለማሰኘት ወይንስ . . . . ? ሌላው ቢቀር ማርክስና ኤንግልስ በኰሚኒስት ማነፌስቶ አድኃሪ ሶሻሊዝም ጉልተኛ ፤ ንዑስ ከበርቴና ጀርመን ወይንም «እውነተኛው» ሶሻሊዝም፤ . . . . ወዘተ እያሉ የጻፉትን አቶ ኃይሌ አላዩም አልሰሙም። የናዚ ፓርቲ በሶሻሊዝም ሥም ጸረ ማርክሲስት ያውም እጅግ ቀኝ ክንፍ የሆነ (አቋም እንደ ነበረው አላውቁትም ወይስ ..........? እሺ ይህ ይካድ በአሁኑ ወቅት በአረብ ብሔረተኝነት ላይ የተገነባው አረብ ሶሻሊዝም ማርክሳዊ ሌኒናዊ ይሆን? ለአቶ ኃይሌ መሆኑ ነው። የኑሜሪ ሱዳን ሶሻሊስት ነኝ እኮ ነው የምትል። ስንት ማርክሳዊ እንደታረደ ግን የማያውቅ ቢኖር እሱ ማን ነው ? ማርክሲዝም - ሌኒንዝም አንድ ብቻ ነው እሱም ሳይንሳዊ ሶሻሊዝም ነው። መቸም አቶ ኃይሌ ከመጀመሪያ የሳቱት (የለቀቁት) ጎዳና ከዚህ ስህተት ቢጥላቸው አይገርምም። ፍልስፍና ሁሉ ሳይንስ ነው ከዚያ ቀጥሎ ሶሻሊዝም ሁሉ ማርክሳዊ ሌኒናዊ ነው በዚህ ጎዳና የተጓዘ ቀጥሎ የሚለው ድህነትን ያመጣው ሰው ነው። ሰው ድህነትን ያጠፋዋል .................. አዲዮ! ኃይሌ ፊዳ በቀኝ ማርክሲዝም ሌኒኒዝም በግራ። 


ከጥቅሱ ሁለተኛውን እንውሰድ « .... የሰው ልጅ እውቀት ባደገ ቁጥር ከዚያ እየተመገበ ፤ እየዳበረ የሚሄድ ነው» ኃይሌ ፊዳ። «ተግባራዊ አንድነትን በሚመለከተው ረገድ እነዚህ በማቴሪያሎች (ማለትም በአንድ በኩል የምርት ኃይሎች በሌላ በኩል የአብዮታዊ ሰፊ ሕዝብ መኖር ) አጠቃላይ አብዮታዊ ሁናቴ ከሌለ አብዮታዊ «አስተሳሰብ» መቶ ጊዜ መደጋገሙ ዋጋ እንደሌለው የኮሚኒዝም ታሪክ ያስረዳናል» ጀርመን አይዲዬሎጂ ገጽ ፳፱ ማርክስናን ኤንግልስ። ለማርክሲዝም ሌኒኒዝም እድገት ዋናው ምንጭ የአንድ የተወሰነ የምርት ኃይል እድገት ደረጃና የአብዮታዊ ሰፊው ሕዝብ መሆኑ ቀርቶ «ከሰው ልጅ እውቀት እየተመገበ» ያደገና የሚያድግ አድርጎ የሚያቀርበውን የኃይሌ ፊዳን ጥቅስና ሳይንሳዊ መሰረት ያለውን የማርክስና የአንግልስ ጥቅስ አወዳድሩና አንባቢያን ፍረዱን። ማርክሲዝም ሌኒኒዝምን ከሕብረተሰቡ ገንጥሎ ከሰው ልጅ «እውቀት» እየተመገበ የሚኖርና የሚያድግ አድርጎ መለኰታዊ ኃይል መስጠት የከበርቴ አፈቀላጤዎች የሚያደርጉት ፌዝ ነው። ይህስ ማስተማር ነው ማወናበድ? 


ከዚህ ቀጥሎ በገጽ ፫ ለቲዎሪ የተሰጠውን ትርጉም እንዲሁ ኃይሌ ፊዳ ያሉትን አስቀ ምጦ መሳቁ ይሻላል። «ቲዎሪ ማለት ገና በሥራ ያልተፈተነ አጠቃላይና የተቀነባበረ እውቀት ነው። በመሰረቱም ተግባር (የፕራክቲስ) መመሪያ ነው። ያለቲዎሪ ተግባር! ያለተግባር ቲዎሪ ሊኖር አይችልም።» 


አቶ ኃይሌ ፊዳ ከዚያ ከዚህ እየቀነጠቡና እየበጠሱ እንዲሁም የእራሳቸውን ተራ እውቀት እየቀጠሉ በመደንጎር የሚያወናብዱን በማቴሪያሊዝምና (ቁሳአካልነት) በአ ይዲያሊዝም ሕሊናዊነት ትንተና ነው። ለምሳሌ ስለ መብረቅ አመጣጥ ከሁለቱ የፍልስፍና ፊናዎች አንዱ ቁስአካላዊ ፍልስፍና የሚሰጠውን አስተያየቶች ሲጠቅሱ «መብረቅ የሚመጣው በደመና ውስጥ በልዩ ልዩ አካባቢዎች ሁለት የተለያዩ ጠባዮች ያሏቸው የኤሌክትሪክ ኃይሎች ሲፈጠሩ ነው። ምን ዓይነት ማቴሪያሊስት ይሆን አቶ ኃይሌን ያጋጠማቸው? ይህን ያሉ ሁሉ ማቴሪያሊስት ከሆነ የቡርዣዎና የፊውዳል ሊቃውንት (ሳይንስቲቶች) በሙሉ ትርጉሙ ሊሆኑ ነው ማለት ነው። ይህ መቸም በጣም ማወናበድና ሰፊው ሕዝብ ለማቴሪያሊዝም የሚሰጠውን ትርጉም በአይዲያሊዝም ለመበረዝ መነሳት ነው። ሌላው ምሳሌ ደግሞ በገጽ ፲፬ እና ፲፮ የሚገኘው ስለ ኃብት አከፋፈል የተሰጠው በጣም አሳዛኝና አስቂኝ ምሳሌ ነው « በቁሳ አካላዊ ርዕዮተ ዓለም የሚያምነው........ እንግዲህ ወደ መሰረቱ ስንሄድ እግዚአብሔር ምድር ወርዶ መሬት ያከፋፈለበት ምንም ጊዜ አልነበረም። የእርሻን መሬት በጥንት ዘመን የተከፋፈሉት የተወሰኑና ጉልበት የነበራቸው ቤተሰቦች ነበሩ። የሕብረተሰቡን የተፈጥሮ ሀብት በማዳላት የደለደለውና ብልጽግናና ድህነትን የፈጠረው ሰው ራሱ ነው። ሊለውጥውም የሚችለው ሰው ራሱ ነው።» ይኸን ምሳሌ ለሁለት ከፍለን እንየው። አንደኛ ፤ ሕብረተሰቡ በመደብ በመከፋፈል የኃብት ልዩነት ተፈጠረ ያለውን ሁሉ ማቴሪያሊስት አድርጎ መቁጠር አንድም ማቴሪያሊዝም አለማወቅ ወይንም ለማሳሳት ቆርጦ መነሣት ነው። 


ሁለተኛውና በጣም አወናባጅ የሆነው ነገር በጥቅሱ ውስጥ ያሉትና ሌሎቹ በጣም አሳሳች የሆኑት እምነቶች ናቸው «ድህነትን የፈጠሩ ሀብታሞች ናቸው» ገጽ ፲፭ «ብልጽግናን ድህነትን የፈጠረው ሰው ራሱ ነው። ሊለውጠውም የሚችለው ሰው ራሱ ነው ።» ይህ መቸም አይንን ጨፍኖ ማርክሳዊ ሌኒናዊውን የሕብረተሰብ ትንተናን መካድ ነው። የሰው ልጅ በራሱ ፍላጎትና ምኞት የፈለገውን ዓይነት የምርት ግንኙነት ይፈጥርና ሲያስፈልገውም የሚለውጥ አድርጎ በማቅረብ ግልጽ የሆነውን ሕሊናዊ አስተሳሰብ ለቁስአካላዊ ፍልስፍና ምሳሌነት አቅርበዋል። የሕብረተሰብ የታሪክ እድገት እንደሚያሳየን አንድን ሥልተ ምርት የሚፈጥረው በምርት ኃይሎችና በምርት ግንኙነት መካከል ያለው ቅራኔ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ የሚካሄደው የመደብ ትግል ነው። ሰዎች ይሀንን ወይም ያንን ሥርዓት እንመሥርት ቢለው በስምምነት ወይም በአንዳንድ «ታላላቅ» ሰዎች ኃይል የሚመጣ ነገር አይደለም። እንደ ኃይሌ ፊዳ አባባል (ድህነትን የፈጠሩ ኃብታሞች ናቸው) ጭሰኛን የፈጠረው ጉልተኛው ነው ፤ ላብአደሩን የፈጠረ ከበርቴው ነው ወዘተ ከዚያ ቀጥሎ ድህነትንና ብልጽግናን የፈጠረው ሰው ነው (በላይኛው ዓይነት ጉልተኛው ከበርቴው ወዘተ) የሚያጠፋው ሰው ነው ማለትም የባሪያው ገዥ ጉልተኛው ከበርቴው ድህነትን የሚያጠፋ መሆናቸው ነው። ይህ አስተሳሰብና ማርክሳዊ ሌኒናዊ ፍልስፍና ምንም የሚያገናኛቸው ነገር የለም። እንዲያውም የማርክሳዊ ሌኒናዊ ፍልስፍና ተጻራሪ ቁልጭ ያለ አድኃሪ አስተሳሰብ ነው። ከዚህ ሌላ ከምሳሌዎቹ የምንረዳው ኃይሌ ፊዳ በባላባታዊ ባህል የተተበተቡና በተለመደው አድርባይነት ጸባይ «ክርስቲያኑን የኢትዮጵያ ሕዝብ» ላለማስቆጣት «እግዚአብሔርን» ምድር ወርዶ (ወይም እንደሳቸው አስተሳሰብ ቁስአካላዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ያልገባ) በሰማየ ሰማያት የተቀመጠ መንፈስ መሆኑን ደጋግመው ጽፈዋል። ለምሳሌ « . . . . .እግዚአብሔር ምድር ወርዶ መሬት ያከፋፈለበት ዘመን የለም» (ሰማይ ላይ ሆኖ ግን አከፋፍሏል ለማለት ነው?) ይህን መቸም የሚል ማርክሳዊ ሌኒና ሳይሆን ቄስ የመሬት ይዞታ ሹም (በአሁኑ ጊዜ ካለ) ብቻ ነው። «በቁስአካላዊ ርዕዮተ ዓለም የሚያምኑ ሰዎች የመብረቅን አመጣጥ ለማወቅ ሩቅ ሳይሄዱ ምክንያቱን እዚሁ በአካባቢያችን በቁስአካላዊ ዓለም ውስጥ መፈለግ አለብን ፡ ወደ እግዚአብሔርና ሰይጣን ለመሄድ ምንም ምክንያት የለንም ይላሉ።» ይህ እንኳ የሚያሳየን አቶ ኃይሌ ፊዳ «እግዚአብሔርን» ያለኃጢአቱ አትሙት የሚሉ ፈሪሐ እግዚአብሔር ያደረባቸው ምሁር መሆናቸውን ብቻ ነው። 


ከዚህ ቀጥሎ ያለው ስህተት ደግሞ ዋናና መሰረታዊ የፍልስፍና ጉዳይ ነው። «ቁስአካላዊ ርእዮተ ዓለምን የሚከተሉ ሰዎች የሚጠቀሙበት ብዙውን ጊዜ ዲያሌክቲክስ የተባለ ዘዴ ሲሆን የሕሊናውያን ርዕዮተዓለም የሚከተሉ ደግሞ ሜታፊዚክስ የተባለ የአሰራር ወይንም የአቀራረብ ዘዴ ይከተላሉ» ከዚህ ጥቅስ «የምንማረው» አንደኛ ቁስአካላዊ ሁሉ ዲያሌክቲካዊ አመለካከት አለው ሕሊናዊ ሁሉ ሜታፊዚካ አመለካከት አለው የሚል ይሆናል። ግን በዚህ ፍልስፍና ታሪክ ተጣሰ። ማርክሳዊ ትንተና ተደለዘ። በአንደኛ ደረጃ ዲያሌክቲካዊ አመለካከትን መጀመሪያ ሳይንሳዊ መልኩን የሰጠው ሕሊናዊ ፈላስፋ ሔግል እንደሆነ በመጽሐፉ ተጠቅሷል (ገጽ ፳፪) እንደገና መልሶ የማቴሪያሊስቶች ዘዴ (ብዙውን ጊዜ) አድርጎ ማቅረብ ምን አይነት መለሳለስ ነው? አቶ ኃይሌ ከነ ማርክስ በፊት የነበሩ በጣም ብዙ ቁስአካላዊ ፈላስፎች አመለካከታቸው ሜታፊዚክሳዊ ነበር። ለምሳሌ እንደነ ዴስካርተስ፣ ስፒኖዛ፣ ቤከን የመሳሰሉት የ፲፯ኛውና ፲፰ኛው መቶ ዘመን ፈላስፎች ሜታፊዛካዊ አመለካከት ነበራቸው ፣ ነገር ግን ሕሊናዊያን ሳይሆኑ ቁስአካላዊ ፈላስፎች ነበሩ። 


በገጽ ፴፪ ላይ ስንደርስ ደግሞ ሜታፊዚክስ የአመለካከት ዘዴ ፤ ነገሮችን የአቀራረብ መንገድ መሆኑ ቀርቶ የፍልስፍና ዘርፍ ይሆናል። «የሜታፊዚክስ ፈላስፎች» ይላሉ ኃይሌ ፊዳ። ከየት የመጣ ዘርፍ ነው ደግሞ ይኸ? ወይንስ ሕሊናዎች ከተባለ ሁሉም ሜታፊዚካሊ ይመለከታሉ ለማለት ይሆን። መቸም በሁለቱም በኩል ከፍተኛ ስህተት ነው የተሰራው። ሜታፊዚክስ የአመለካከት ዘዴ እንጅ የፍልስፍና ዘርፍ አይደለም። 


« ......... ሕሊና ሲባል የማሰብን ችሎታ ወይም ባሕርይ ማለት ነው። ሰውን ከእንሰሳ የሚለየውን የመገንዘብ ፡ የማሰላሰል ፤ የማወቅ ችሎታ ነው » 


የዚህ ጥቅስ ትርጉም አንደኛ ሕሊና የማሰብ ባሕርይ ወይም ጠባይ ሲሆን በሁለተኛ ደረጃ ሰው ከአንሰሳ የሚለየው በማሰላሰሉና በመገንዘቡ ነው ማለት ነው። ይህ ሳይንስን ይቃረናል ፤ የማርክሳዊ የፍልስፍና መሰረትን ይቃረናል። ሕሊና የአንጎል ባሕርይ ፤ ጸባይና ተግባር (ኮንሾየስነስ የአንጎል ፕሮፐርቲ ነው) እንጅ ሕሊና የማሰብና የማሰላሰል ባሕርይ አይደለም። ሕሊና የማሰብና የማሰላሰል ባሕርይ ከሆነ በቀጥታ ቀዳማይት (ከቁስአካል) ያለው መሆኑን መቀበልና ሕሊናዊ ፍልስፍናን መስበክ ነው። 


የጥቅሱ ሁለተኛውን ክፍል እንውሰድ « .........ሰውን ከእንሰሳ የሚለየው የመገንዘብ ! የማሰላሰል የማወቅ ችሎታ ነው » ይህ የመገንዘብ ፤ የማሰላሰልና የማወቅ ችሎታ ሰውና እንሰሳን የሚያመሳስላቸው እንጂ የሚያራርቃቸው የሚለያቸው አይደለም። እንሰሳት የተፈጥሮን ሁናቴ ብርድን ፣ ሙቀትን ፤ ርኃብን ፤ ፍትወተ ሥጋን ወዘተ ይገነዘባሉ ያውቃሉ፤ ሰውም እንዲሁ። ሰውንና እንሰሳን የሚለያቸው ዋናው ነገር ሰው ተፈጥሮን እንደገና ለራሱ ጥቅም ሲያውላት እንሰሳት ግን ለጊዜው (ለወዲያው) ተፈጥሮን ተጠቀመው እንደገናም መልሰው በተፈጥሮ (ኔቸር) ሥልጣን ሥር በመሆን ይቆያሉ። ይህን ልዩነት የፈጠረው ማሰብ ሳይሆን «ሥራ» ነው ኤንግልስ ስለዚህ ጉዳይ ሲያስረዳ «በአጭሩ እንሰሳት አካባቢያቸውን ብቻ በመጠቀም የሚያመጡትም ለውጥ ፤ ያው የራሳቸውን መኖር ብቻ ነው ፤ ሰው ግን በመለወጥ የራሱን ፍላጎት ያሟላበታል ፣ በቁጥጥሩም ሥር ያደርገዋል። ይህ ነው በሰውና በእንሰሳ መካከል ያለው የመጨረሻውና ዋናው ልዩነት ፤ ይህንን ልዩነት ያመጣው ሥራ ነው።» የአቶ ኃይሌ ሰውና እንሰሳን ሕሊናቸው ይለያቸዋል መጽሐፍ ቅዱስ (ኃይማኖታዊ) በዚያውም የሕሊናዊያን አገላለጽና አደናጋሪ ነው። 


የኃይሌ ፊዳን የመጽሐፍ ይዘትና አቅጣጫ እንዲሁ በአንድ ዓይነት መንገድ ተመልክቶ ከመውሰድ በሁለት ከፍሎ ማየቱ አስፈላጊ ነው ። አሁን በዚህ ጽሑፍ ያየነው አይነተኛና መሰረታዊ ሥህተቶችን ሲሆን በሚቀጥለው ክፍል ደግሞ የዚህን «ፍልስፍና» የፖለቲካና የሶሻል አቅጣጫ እንመለከታለን። 


ቀጣዩ ክፍል 


ከምዕራፍ ሶስት (ገጽ ፷፯) ጀምሮ እስከ መጽሐፉ መጨረሻ ደራሲው ያተኩሩት በታሪክ ቁስ አካልነት (ማቴሪያሊዝም) ላይ ሲሆን አሁንም አንዳንድ ጠቃሚ ትምህርቶችን እየሰጡ አንዳንድ አደናጋሪ ሐሳባችን ወርውረዋል። ገጽ ፸፭ ላይ ስለምርት (ፕሮዳክሽን) በሚያስረዱበት ወቅት « . . . ማንኛውንም የተጨበጠ የሥራ ፍሬ የሚሰጠውን ሁሉ ድርጊት ነው ብለዋል። «ሶሻል ተፈላጊነት» የሚል ሐረግ ማስገባት በተገባ ነበር። ሶሻል ተፈላጊነት የሌለውን ማለትም የግልጋሎት ሆነ የለውጥ ዕሴት የሌለውን ማናቸውንም ቆሳቁስ ሆነ አገልግሎት ማምረት ፕሮዳክሽን አይሆንም (ካፒታል ቅጽ ፩ ተመልከት) ይህ አነስ ያለ ግድፈት ነው ዝቅ ብሎ ገጽ ፷፯ - ፷፰ ላይ ስለምርት ግንኙነት ሲዘረዝሩ ግንኙነቱ የትብብር ወይንም የጨቋኝ የተጨቋኝ ሊሆን እንደሚችል ገልጸው ይህ የሚወስነው « የምርት ማከናወኛዎቹ (ማምረ ቻዎች) ባለቤት ማነው ለሚለው ጥያቄ የሚሰጠው መልስ ነው » ብለዋል ። አብሮ መጠቆም የነበረበት ዓቢይ ጉዳይ የማምረቻዎች የዕድገት መጠን ከምን ላይ እንደሚገኝ ጭምር ነበር። ይህ ቢጠቀስ ኑሮ የዚህ ዓይነቱንም (ማለትም የኅብረትና የወንድማማችነት ..... ወዘተ) ግንኙነት ለመፍጠር መደቦችን ማጥፋት ስለሚያስፈልግ ትግሉ የረጅም የታሪክ ዘመናት ትግል ይሆናል» በማለት የኰሚኒስቱን ሥርዓት ብቻ በመተንበይ ከመደቦች መፈጠር በፊት በጋርዮሽ ዘመን የነበረውን ተመሳሳይ የምርት ግንኙነት ባልዘነጉም ነበር። በዚሁ ገጽ ላይ ደግሞ የመጨረሻው አንቀጽ ትርጉም ሊኖረው ይችል የነበረው ፤ 


ሀ/ ገለጻው ከሃያ ገጾች በኋላ (ማለትም ስለ መደቦች ከተሰጠው ትምህርት) ቢመጣ ኑሮ ፤ 


ለ/ ጉዳዩ እንዳቀራረቡ በግለሰብ ሳይሆን በመደብ ቢታይ ኑሮ (የምርት ማከናወኛውዎች ባለቤት · · አስተዳዳሪ ነው ነው ገዢና የኅብረተሰቡ አቀነባባሪ ነው የሚለው በመደብ ካልቀረበ እጅግ አስቂኝ ይሆናል) 


ሐ/ መሰረታዊና መሰረታዊ ያልሆኑ መደቦች ተለይተው ካልቀረቡ የተሰጠው መንደርደሪያ (የምርት ማከናወኛዎች ባለቤትነት) ከሚከተለው ሹመት ጋር ላይዛመድ ይችላል። ለም ሳሌ ንዑስ ከበርቴው የምርት ማከናወዎች ባለቤት ነው ግን « የበላይ ነው አስተዳደሪ ነው ባለ ሥልጣን ነው ገዢና ለኅብረተሰቡ አቀነባባሪ ነው ማለቱ ግፋ ቢል የኃይሌ ፊዳን ምኞት ይገልጻል እንጂ ነባራዊውን ሁኔታ አያመለክትም። በነገራችን ላይ እንዳጋጣሚ ይህ ሰሞኑን ባንዳንድ ሥፍራዎች እየታየ ነው። 


ገጽ ፰ ገጽ ፹፪ና ፹፫ ላይ ያልናት ያች ማደናገር ብቅ ብላ ትመጣለች። ስለጥንታዊው ሰው የምርት ማከናወኛዎቹ ያለፉባቸው የተለያዩ የዕድገት ደረጃዎች (ድንጋይ ቀስት ብረት ወዘተ) ከተጠቀሱና አደን ሶሻል ተግባር እንደሆነ ከጠቀሱ በኋላ (ከዛ በፊት የነበረው ሥራ ለምሳሌ ገና ድንጋዮችን መሳል ሲጀመር እንደምን ሶሻል እንዳልነበር ምስጢር ሆኖብናል) « .... የተገኘው ቁስአካላዊ ሀብት ለሁሉም ሲዳረስና ሲተርፍ መንደሩ ከሁለት ተከፍሎ አንዱ ክፍል የቀስትና ፍላጻ ሠሪ አንደኛው ደግሞ አዳኝ ሆነ» ተብሏል። ለሁሉም ሲዳረስና ሲተርፍ የሚለው ጥገኛ ሐረግ በጣም ግራ ያጋባል «ሁሉም» የተሰኙት የሚያድኑት ብቻ ሆነው « ሲተርፍ» የተባለው ከነሱ የተረፈውን ከሆነ ሐረጉ አያጣልም « ሁሉም የተባሉት አዳኞችም ባለእጆችም ከሆኑ ሲተርፍ የሚለው ከሕብረተሰቡ የተረፈ መሆኑ ነውና አቶ ኃይሌ መጣላታችን ነው። እንደምን ይበሉ፤ እንደ አጻጻፍዎ ከሆነ ከአደን ፍሳሽ ትርፍ (ትርፍርፍም ይሉታል ሰርፕለስ) ሊገኝ ይችላል ማለት ነው። ይህ እንኳን በያኔው በድንቁርና ዘመን ባሁኑም በቴክኖሎጂ ዘመን የሚቻል አይደለም። ጠበንጃ ይፈልጉና ( በብዛት ማግኘት ይችላሉ) ይሞክሩት እንኳንስ ሰርፕለስ ሊገኝ በሱ ብቻ መተዳደር መቻሉ ያጠራጥራል። የሥራ መከፋፈልን ብቻ ለማሳየት ነው የተናገርኩት እንዳይሉ ለጠቅ አድርገው « ኅብረተሰባዊ የሥራ መከፋፈልም ሲመጣ ሰዎችም ከጋርዮሽ ግንኙነት ወደባለቤትነት ግንኙነት ማለትም ወደመደብ ግንኙነት ተሻ ገሩ » ብለዋል። መደቦች ካሉ የግዴታ ሰርፕለስ አለ ማለት ነውና ! ለነገሩሳ « የሥራ መከፋፈል ሲመጣ...» በቀጥታ መደቦች መች ተፈጠሩና። የጾታውስ የአእምሮና የጉልበት ሥራ መከፋፈሉ ሶሻል ነበሩ (።) በቀጥታ መደቦችን ፈጠሩን ? በፍጹም አይደለም። ራሱ ሶሻል የሥራ መከፋፈል አንድ የተወሰነ ደረጃ ላይ ሲደርስ ነው መደቦች ሊፈጠሩ የቻሉት። ከአደን ሰርኘለስ ይገኛል አላልኩም እንዳይሉ ደግሞ እውነተኛ ሰርፕለስ ፈጣሪ የሆነውን እንቅስቃሴ ግብርናን ያመጡት በገጽ ፹፪ መጨረሻና በገጽ ፹፫ መጀመሪያ መካከል ላይ ብዙ ሺ ዘመናት ከነጎዱ በኋላ ነው ስለመደብ ያወሩት። ግን ይበልጥ የሚያስገርመው ስለጋራ ባለቤትነት መቅረት ገና ግብርና ሳይጀመር ነው ለመደቦች መፈጠር ለንብረት ወደግል መዛወር አብሮም ለመጣው የጨቋኝና የተጨቋኝ ግንኙነት መጀመር ተቀዳሚ ግዴታ በሕብረተሰቡ ውስጥ የሰርፕለስ ምርት መገኘት ሲሆን ይህን መሰሉ ምርት ሊገኝ የተቻለው ግብርና በተለይም ከብት ርቢ ተጀምሮ ከሰነባበተ በኋላ ብቻ ነው። ለጋርዮሽ ሥርዓት መፍረስ ምክንያት የሆነው የምርት ግንኙነቶች መለወጥ ሲሆን ለዚህም ምክንያት የሆነው የምርት ማከናወኛዎች (ማምረቻዎች አብዮታዊ የሆነ ለውጥ በማሳየታቸው ነው። ይህም አብዮታዊ ለውጥ የአዲሱ ድንጋይ ዘመን አብዮት (ኒዎሌቲክ ሬቮሎሽን) እየተባለ የሚጠራው በግብርና መገኘት ነው። አደንና ፍላፃ ሰሪዎች በፈጠሩት ሶሻል የሥራ መከፋፈል ሳይሆን እርሻና ክብት ርቢ ተብሎ በተከፈለው እንቅስቃሴ ነው ሰርፕለስ የተፈጠረው ፤ ሥርዓትም ሊለወጥ የቻለው። ይህ ማደናገሪያ ቁጥር አንድ (በምዕራፍ ሶስት) መሆኑ ነው። 


ማደናገሪያ ቁጥር ሁለት ባሪያዎችን የሚመለከት ነው። ገጽ ፹፫ ላይ እንዲህ ተብሏል « ከብዙ ሺ ዘመናት በኋላ መሬትን ማረስ ሲለማመድ አንዱ መንደር በሌላው ላይ ዘመቻ እያደረገ የማረከውን ሰው ባሪያ እያሰኘ ወደምርት መሣሪያነት ለውጦት እራሱን ያሰራው ጀመር። በአንድ ዓረፍተ ነገር ውስጥ ሁለት ስህተትና አንድ ግድፈት (ኦሚሽን) አሉ። የመጀመሪያው ስህተት ለባርነት መጀመር መሬትን ማረስ ማስመስሉ ነው። ሰርፕለስ በመጀመሪያ የተገኘው ከእርሻ ሳይሆን ከከብት እርቢ እንደሆነ ሞርጋንና ኢንግልስ ባይነግሩንም ኑሮ በተራ ማሰላሰል የምንደርስበት ሐቅ ነው። ስለዚህም የመጀመሪያዎቹ ባሪያዎች ምናልባት እረኛ እንደሆኑ በቂ የአካባቢ ማስረጃዎች ተገኝተዋል። (ኤንግልስን የቤተሰብ የግል ንብረትና የመንግሥት አመጣጥ ፤ አረማዊነትንና ሥልጣኔ የሚለውን ክፍል ፱ መመልከት ይበጃል ) ሁለተኛ ስህተት ከመጀመሪያውም ባርነትና ዘመቻን (ምርኮን) አንድ ማድረግ ወረራ እያደረጉ ምርኮን ባሪያ ማድረግ የተጀመረው ባርነት ተጀምሮ ከቆየ በኋላ ነው። እማዊ ሥርዓት (ማትሪያርካል) የከብት እርቢ በፈጠረው የሰርፕለስ መገኘት ተገርስሶ በአባዊ ሥርዓት ( ፓትሪያርካል) ከተተካ ጊዜ ጀምሮ ባርነት ቤተሰብ ውስጥ ይገኝ ነበር። የመጀመሪያው ባርነት ቤተሰብ ውስጥ ሲጀምር የመጀመሪያውም ጌታ አባወራው ነበር የምርት ግንኙነቱ ቀስ በቀስ እየተለወጠ ሲሄድ ማምረቻዎምች ቀስ በቀስ ወደ ጥቂቶች እጅ መግባታቸውን ቀጠሉ ። ባርነት ከቤተሰብ ወጥቶ በዘመድ አዝማድ አካባቢ ፤ ለጥቅም በኰሚኒቲው ውስጥ ሊስፋፋ ቻለ። ዘመቻው የመጣው ከዚህ በኋላ ነው። ግድፈት የተባለው ባርነትን ከሰርፕለስ ጋር ባርነትን ከቦታ ጥበትና ከሠራተኛ እጥረት ጋር አለማያያዙ ነው። ዲያሌክቲክስ ከተባለ ላይ ላዩን መፈንጨት ሳይሆን በመጠኑም ቢሆን ማናቸውንም ሁኔታ እያስተሳሰሩና በተቃራኒ መስኰቹ ማቅረብም ጭምር መሆን አለበት። ይህ ለማስታወስ ያህል ነው ስለባርነት ካወራን አይቀር ኦቶ ኃይሌ - ስለባሪያ ሥርዓት አወዳደቅ የሰጡት መግለጫ ውሃ ውሃ አሰኝቶናል። ለሮማውያን ሥልጣኔ አወዳደቅ ምክኒያቶች ሲሰጡ የባሪያው መደብ አመጽና የውጪ ወራሪዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። ለሁለት መቶ ዓመታት ባንድ ፊት በባለባሪያዎች በሌላ ፊት በነጻ ሰዎች (ባሪያ ያልሆኑ ግን ባርነት መፈናፈኛ የነሳቸው ደሀ ባለመሬቶችና በፕሮሊቴሪያን (የከተማ ሸቃዮች) መካከል የተካሄደው የርስበርስ ጦርነት (የመደብ ጦርነት) መሠረታዊ መሆኑ ተዘንግቶ ይሆን ? ኃይሌ ፊዳና ቶይንቤ ተመሳሰሉ። ቶይንቤ ደግሞ ሕሊናዊ ነው። 


« የከበርቴውን ስልተምርት ዓይነተኛ የሚያደርገው የምርት ማከናወኛዎች የከበርቴው መደብ መሆናቸውና ወዛደሩ ያለጉልበቱ የሚሸጠው ነገር አለመኖሩ ነው። » ርግጥ ይበልጥ ዓይነተኛ የሚያደርገው ግን በማምረቱ ተግባር ተሳታፊ የሆኑት ሁለት ወገኖች (ማለትም አሰሪና ሠራተኛ) በመካከላቸው የሸቀጥ ግንኙነት ማበጀታቸው ነው። ለአሰሪው ከበርቴ ማምረ ቻዎች ሸቀጥ ሲሆኑ ለሠራተኛው ላባአደርም ጉልበቱ ሸቀጥ ነው። ከተቀሩት ሶሻል ሥርዓ ቶች ካፒታሊዝምን የሚለየው ይኸው ነው። « ወዛደሩ ሠርቶ የሚያስገኘውን የምርት ውጤት ከበርቴው በትርፍ ሸጦ የሀብቱን ይዘት ያስፋፋ በታል » የሚለው ዓረፍተ ነገር ላለንበት ሁኔታ በቂ ቢሆንም ሳይንሳዊ ትንተና ተብሎ ከቀረበ ስህተት ይሆናል። ምክንያቱም ትርፍ የሚገኘው በሽያጭ ላይ ሳይሆን ከሽያጭ በፊት ነው። ከበርቴው በማዕከላዊ አነጋገር የሚሸጠው በትርፉ ሳይሆን በወጪው ነው። ይህ እንኳን እምብዛም የሚያስወቅስ አይሆንም። የፖለቲካ ኢኮኖሚ መጽሐፍ ባለመሆኑ ፤ የኃይሌ ፊዳን የፖለቲካ ኢኮኖሚ ዕውቀት ግን ያጋልጣል። 


በምዕራፍ ፫ ክፍል አምስት መደቦችና የመደቦች ትግል በሚለው ርዕስ ሥር የቀረበው ትንተና ከሞላ ጎደል ጠቃሚ ቢሆንም ገጽ ፻ ላይ አሁንም አንድ ሌላ ማደናገር ተፈጽመዋል። ጸሐፊው አንድ ሬቮሎሸናዊ መደብ ትግሉን እንደምን ማካሄድ እንደሚገባው ከተነተኑ በኋላ «አቤቱታን በማቅረብ የፓርላማ አባሎችን በመምረጥ ወ.ዘ.ተ. ከተወሰነ ፤ እንኳንስ የመንግሥት ሥልጣን ለመያዝ ቀርቶ ቁስአካላዊ ጊዜያዊ ፍላጎቶቹን እንኳን ለማርካት ፈጽሞ አይቻልም» የሚል «ማስጠንቀቂያ» ሰጥተዋል። ጉዳዩ የሚንጠለጠለው ጌዜያዊ ፍላጎቶች በሚለው ላይ ነው ቀደም ሲል ስለትግል ሲያወሱ ኤኰኖሚያዊና ፖለቲካዊ ብለው ለይተው ነበር። ኢኮኖሚያዊ የሚለውን በቅጡ ባይተነትኑትም ለደሞዝ ዕድገት ለሥራ ሰዓት መቀነሻ : ለጥቅማጥቅሞች መገኘት ወ. ዘ. ተ. የሚደረገው ትግል እንደሆነ በውስጠ ታዋቂነት የምንረዳው ነው። ይህ ትግል « ጊዜያዊ ፍላጐቶች » ለማርካት የሚደረግ አይደለምን ? በዚህ ዓይነቱ ትግል ጊዜያዊ ፍላ ጎቶች እንደሚረኩ የመላው ምዕራብ ዓለም የሙያ ማኅበር እንቅስቃሴ (ትሬድ ዩኒየንኤዝም) ምስክር አይሆንምን ? ጥገናዊ ለውጥ ምን ሆነና! በመሠረተ ሐሳቡ እንስማማለን በኢኮኖሚዝም የመንግሥት ሥልጣን እንደማይያዝ አምናለሁ። ግን ጊዜያዊ ቁስአካላዊ ፍላጐቶችን ለማርካት ፈጽሞ አይቻልም የሚለውን ቀኖናዊ አባባል አልቀበልም። « ሲመክር ብርቱ ለራሱ ከንቱ » ሆነና « ከተወሰነ » ያሉት ሐረግ ከግራ ቀደምትነት ቢያድናቸውም « ፍጹም አይቻልም » የሚለው ከቀኖናዊ አድርባይነት ካምፕ አሰልፏቸዋል። 


ማጠቃለያ፤ 


በመጀመሪያው ክፍል (ጎሕ ፪ኛ ዓመት ቁጥር ፫) መግቢያ ላይ እንደተጠቀሰው ሙከራው የሚያስመሰግን ቢሆንም በውስጡ ያሉት ስህተቶች ከማደናገርም አልፈው በአንደምታቸው (ኢምፕሊኬሽንስ) አድሀሪና ፍጹም ኢሳይንሳዊ ወደ ሆኑ አቅጣጫዎች ይመራሉ። ለምሳሌ « ያለቲዎሪ ተግባር ያለተግባር ቲዎሪ ሊኖር አይችልም » የሚለውን ገጽ ፫ ላይ በሕዳግ ማስታወሻ (ፉትኖት) ያሰፈሩትን እንመልከት የዚህን አባባል አንደምታዎች እንመልከት ፤ እንደ አቶ ኃይሌ አባባል ከሆነ ቲዎሪ በታየ ቁጥር ተግባርም አለ ፤ ተግባር በታየ ቁጥርም ቲዎሪ አለ። እነ ሊቀ መንበር ማኦ ፤ ቲዎሪና ተግባር መገናዘብ አለባቸው ያለቲዎሪ ተግባር ብቻውን እውር ነው ወ. ዘ. ተ. የሚሉትን ሲቃዡ መሆኑ ነው። ምክንቱም አቶ ኃይሌ « ተግባር ብቻውን አይኖርም ሁልጊዜ ከቲዎሪ ጋር ይሄዳል ብለዋልና። ይህ ማርክሲዝም ሌኒኒዝም አይደለም። ማርክሲዝም እንደሚያስተምረው ማናቸውም ቲዎሪ የሚመነጨው ከተግባር ረቆ (አብስትራክት) በመውጣት ሆኖ በተራው ለሚቀጥለው ተግባር መመሪያ ይሆናል። የቲዎሪና ተግባር አንድነትና አለመነጣጠል እስከዚህ ድረስ ነው። ቲዎሪ ከተግባር የሚመነጭ ቢሆንም ሁልጊዜ ትክክለኛ ላይሆን ይችላል። ተግባርን በትክክለኛ መልኩ ሳይረዱ የሚወጣ ቲዎሪ አለ። ቲዎሪነቱ አይካድም ግን በተግባር ሊውል አይችልም። ከከበርቴ ቲዎሪዎች እጅግ ብዙው የዚህ ቢጢ ናቸው። በቀዳማይ አመጣጣቸው ቲዎሪና ተግባር አይለያዩም። በተከታይ ግን ተለያዩ ማለት ነው። ቲዎሪና ተግባር የማይለያዩት ዲያሌክቲካዊ መተሳሰር የሚያበጁት ተግባር በነባራዊ መልኩ ታይቶ ሐቀኛ ቲዎሪው ሲታወቅ ብቻ ነው። ይህ ደግሞ ሁሌ አይፈጸምም ቡርዥዋ ሳይንስና ቡርዥዋ ሶስዮሎጂን የተመለከተ ቲዎሪ ከተግባር እንደሚመነጭ ቢገነዘብም በተራው ተግባርን ሊሠራ የማይችልበት ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚችል ይገነዘባል። ባንጻሩ ደግሞ በጭፍን ብቻ የሚመራ ተግባር ሊኖር እንደሚችል ቲዎሪ አልባ በመሆን በመደናበር የሚካሄድ ተግባር ዘወትር የሚታይ እንደሆነ የሚካድ አይደለም። ቲዎሪና ተግባር አብረው ይሂዱ ቲዎሪ ብቻውን ከሆነ ትርጉም የለሽ ይሆናል። ተግባርም ብቻውን ከሆነ የእውር ጉዞ ነው የሚባለው አነጋገር አንዱ ከሌላው ተነጥሎ « ሊገኝ መቻሉን እያስገነዘብን ፍሬ ያለው ውጤት የሚገኘው ግን ሁለቱ ሲዋሃዱ እንደሆነ ያስተምረናል። « የሕብረተሰባዊነት ፍልስፍና ማርክሲዝም ሌኒኒዝም ይባላል። ፊውዳል ሶሻሊዝም የሚባል እንኳን አለ። የከበርቴ ሶሻሊዝምም አለ። መለዮው ሶሻሊዝም የሚለው ቃል ሳይሆን ሳይንሳዊ የሚለው መሆን ነበረበት፤ ዓላማው ማስተማር ከሆነ። 


ሌላ ጎልቶ የሚታየው ማደናገር እግዚአሔርን በሚመለከተው ረገድ ነው ። አቶ ኃይሌ የሚጽፉት የቅስቅሳ ጽሑፍ ይሁን የፍልስፍና ማስተማሪያ ለመለየት የቻሉ አይመስልም። «እግዚአብሔር ምድር ወርዶ መሬት ያከፋፈለበት ዘመን የለም» የሚባለው አነጋገር ጭቁን ሃይማኖተኞቾን ለመቀስቀስ ጥሩ ዘዴ ይሆን ይሆናል ። ፍልስፍና መጽሐፍ ላይ ግን ጥሩ ማደናገሪያ ነው። ማቴሪያሊዝ ምን ሲሰብኩ ውሎ የማተርን ተቀዳሚኒት ሲያስረዱ ሰንብቶ ፣ እግዜር እንዲህ አይሠራም ፤ እግዜር በዚህ አያገባውም ማለት ታጥቦ ጭቃ መሆን ነው። በስሙ ታክቲክ ተመልሶ ሕሊናዊነት ውስጥ መዘፈቅ ነው። አቶ ኃይሌ ማስተማር ማለት ሁሌ መግባባት ይመስላቸዋል መሰለኝ ተገቢ የሚሆነው ዘዴ ማቴሪያሊስቶች ስለ ፈጣሪና ስለ ሃይማኖት ያላቸውን አስተሳሰብ በቀጥተኛው ሳይንሳዊ መንገድ ከገለጹ በኋላ ወደፊትም (ማለትም በሶሻሊስት ሥርዓት) ውስጥ ምን ዓይነት አቋም እንደሚኖራቸው ማባበያውን ሳይሆን ሐቀኛውን ሁኔታ መናገር ነበር። ታክቲክ ካስፈለገ የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያንን መጥቀሱ ይበቃ ነበር። አማኙን ሕዝብ « ላለማስደንገጥ » ተብሎ ማቴሪያሊስት ፍልስፍናን በአይዲያሊስት እርሾ እያቦኩ ማቅረብ ማወናበድ ነው። ለአይዲያሊስቶች እየተሸቆጠቆጡ ማቴሪያሊስቶችን ማደናገር ፈጣሪ የሚባል ነገር የለም ብሎ በቀጥታ ከመናገር ፋንታ « እግዜር ከሰማይ ወርዶ እንዲህ ሠርቷል እንዲህ አልሰራም እያሉ » እግዜርን በቦታው ከልሎ ማስቀመጥ ምንድነው ? ማርክሲዝም አይደለም ። ኢ አማኒነት (ኢቲይዝም) ከመሆን አንሶ ሊበራ ኢዝም ደረጃ ወርድዋል ። ዘመናዊ ክለሪካሊስቶች ከዚህ የተለየ ይናገራሉን ? ፍራማሶኖ ችስ ? ማስተማሪያ ከተባለ ትምህርት መስጫ ነው። ትምህርት ደግሞ (ያውም የፍልስፍና ትምህርት) ታክቲካል ለመሆን እየተባለ እንዳሻ መጠማዘዝና ፊት ያስተማሩትን ከጥቂት ገጾች በኋላ መልሶ እየሻሩ መሄድ መሆን የለበትም ። ይህ ፈሪህ እግዚአብሔር ብቻ ሳይሆን ፈሪህ ሥር ዓት ጭምር ነው። ይህ ከፖለቲካው ሰልፍ ማሳመር የተወለደ ሕዝብን ባለማወቅና በራስ ባለመተማመን ወተት እየተቀበለ ያደገ እውነትን ለሁኔታው ተስማሚ አድርጎ መኳኳል ነው። እንግሊዞች ፕራግማቲዝም ይሉታል። ፕራግማቲዝም ሕሊናዊ ፊና ነው ። ማርክሲስቶች ደግሞ ፕራግማቲዝምን መቃወም አብዮታዊ ግዴታቸው ነው። ለመሆኑ ኃይሌ ፊዳ ለታክቲክ ብለው ነው ፕራግማቲስት የሆኑት ወይንስ ፕራግማቲስት ሆነው ለታክቲክ ሲሉ ነው ማርክሲስት የሚመስሉት ? መልሱን ከመጽሐፋቸው ብቻ አናገኘውም። መቸም ፕራግማቲስቶች ጭራቸው ቶሎ አይያዝም። «ድህነትን የፈጠሩ ሀብታሞች ናቸው» የሚለውስ ተራ ቅስቅሳ ነው ወይስ ጥልቀት ያለው ትምህርት ? ይችንም ለቅምሻ ያህል እንተንትናት ፤ 


ድህነትን የፈጠሩ ሀብታሞች ናቸው ፥ ሀብት ለድህነት ምክንያት ሆነ ፤ ሀብት ድህነትን ቀዳሚ ነበር፤ደሆች ሳይኖሩ በፊት ዓለም ላይ ሀብታሞች ነበሩ። ታሪክ ባንድ መስኮት ዲያሌክቲክስ በሌላ ወጡና ኃይሌ ፊዳ ባዶ ቤት ታቅፈው ቀሩ። ሀብታሞችንስ የፈጠረ ማነው ? ድሆችን የፈጠረ ማነው ? ሀብታሞች ፤ . . . ትምህርት ቀርቶ ጅዋጅዌ ለመጫወት እረፍት ተደወለ ። ከእረፍት መልስ « ... . . በአንድ በተወሰነ የሕብረተሰብ እድገት ደረጃ ላይ ጥቂቶች ቤተሰቦች ብዙ ኃይል በመጨበጥ ፤ በተፈጥሮ የሁሉም የሆነችውን መሬት የግላቸው በማድረግ ወ. ዘ. ተ. የሚል ትምህርት ቀጠሉ ኃይሌ ፊዳ። ኃይለኞች መሬትን ከደካሞች ነጠቁ ፣ ዘረፉ . . ሀብታሞች ቀማኞች ናቸው ለማለት። ጤና ይስጥልኝ ፕሩድሆን ! ድህነትንም ሀብትንም የፈጠረው ኃይል አይደለም። ኃይል ከጨበጡ በኋላ መሬትን ነጠቁ የሚባሉት እነምኒልክ እንደሆኑ ነው እንጂ ከጋርዮሽ ሥርዓት መጥቀው የግል ንብረት ባለቤት ሆነው ባሪያ መንዳት የጀመሩት ምንጅላቶቻችን አይደሉም። ኃይል የነበረው ሚና ከቁጥር የሚገባ አልነበረም። ለሁለቱም ምክንያት የሆነው በማምረቻዎች ባለቤትነት የተደረገው ለውጥ ነው ፤ ከወል ወደ ግልነት መለወጥ ነው። ለዚ ህም ምክንያት የሆነው የሰርፕለስ መገኘት የፈጠረው አዲስ ዓይነት የምርት ግንኙነት መጸነስ ነው። የመጀመሪያው ሀብታም ባለብዙ ሰርፕለስ የነበረው ሲሆን ኃይልም የመጣው ከዚህ ጋር ተያይዞ ነው እንጂ በቀዳሚነት ምክንያት ሆኖ አይደለም። ይች ንዑስ ከበርቴነት ቶሎ አትለቅ !! 


ባጠቃላይ ስንመለከት አቶ ኃይሌ ዳያሌክቲካዊ ማቴሪያሊዝምንና ታሪካዊ ማቴሪያሊዝምን ማኘክ እንጂ ማመንዥግ የጀመሩ አይመስሉም። አውቀውም ይሁን ሳያውቁት የሕሊናዊነት ፌርማታዎች አሏቸው። በማቴሪያሊዝም ሲጓዙ ይቆዩና ፌርማታቸው አይዲያሊዝም ይሆናል። አንዳንዴ ባለማወቅ ሊሆን ይችላል አንዳንዴ ለታክቲክ ሊሆን ይችላል ውጤቱ ግን አንባቢን ካለማወቅ ላይ መጣል ነው። የቋንቋ አለመለመድ ያሰቡትን ሁሉ አላጽፍ ሳይላቸው አልቀረም ። የመጽሐፉም መጠነኛነት ትንተና ላይ እንዳያተኩሩ አግዷቸውም ይሆናል ስህተቶች አሉ ግድፈቶችም አሉ ፤ ባለመብራራት ወደ ገደል የሚያመሩ ሐሳቦች አሉ። « ሕሊናዊ ርዕዮተ ዓለም ያላቸው ሰዎች እንደሚሉት የሰው ሕሊና ቁስ አካልን የሚፈጥር ሳይሆን ሕሊና እራሱ የቁስ አካል ልዩ ንብረት ነው » (ገጽ ፴፮) የሚል ቅዠትን የመሳሰሉ እንዳይወጡ ክለሳ የሚያስፈልግ እንደሆነ እንጠቁማለን። የጻፉትን መልሶ ማንበብ ከዚህ መሰል የእጅ እላፊ ያድናል። « የሜታፊዚክስ ሊቆች ለቁስአካል አንዳች የመጀመሪያ ፈጣሪ እንደሚፈልጉለት ሁሉ ...» ገጽ ፵፩ የሚለውም ቢታረም የነ ስፒኖዛና ፥ ፊውርባህ ወ. ዘ. ተ. አጽም አይረግሞትም። ገጽ ፵፰ ላይ ተመሳሳይ እርማት ይደረግ። እንዳልኩት ዋና ዋናው ግድፈትና ስህተቶች ተዘረዘሩ እንጂ ከቁንጫ መላላጫ ላውጣ ከተባለ መዓት ይገኛል። ይህ ሁሉ ከታረመ መጽሐፉ በተለይም አቀራረቡ ጥሩ ስልትን የተከተለ በመሆኑ ሊጠቅም እንዲችል ይሆናል።

ስለ ጸሐፊው/ዋ እርሶ የሚያውቁት የተለየ ነገር ካለ፣ እዚህ ሲጠቀስ የጎደለ ነገር ከተሰማዎት፣ አዲስ ተጨማሪ ስራ ሲያገኙም ኮመንት መስጫው እርሶን እየጠበቀ ነው።

Comment

Ads

advert
advert