ደራሲ - ኃይለ ሥላሴ ደስታ (ስራዎቹን ለማየት ስሙን ይጫኑት)
የመጽሐፉ ርዕስ - የሚያቃጥል ፍቅር : እግረ ጸሐይ ከዶክተርነት ወደ ሴተኛ አዳሪነት ለምን ተዛወረች?
ሃያሲ (ተቺ) - ይልማ ሀብተየስ (ስራዎቹን ለማየት ስሙን ይጫኑት)
ጽሑፉ የወጣበት ቦታ - ፀደይ መጽሔት
ዘመን - ግንቦት 1967 ዓ.ም.
✍️✍️✍️✍️✍️
በመሠረቱ አንድ ደራሲ የመሰለውን ፈጥሮ በሕይወት ጉዞ ላይ ሊደርስ በሚችል ሁኔታ በልብ ወለድ መልክ ድርሰቱን ለአንባቢ ያቀርባል። በሌላ በኩል ደግሞ የሆነን ታሪክ መነሻ በማድረግ የራሱን ሀሳብ አክሎ መሠረቱን ሳያናጋ ለሱ በሚስማማው መንገድ አስፋፍቶ ታሪካዊ ልብ ወለድ ሊያደርገውም ይችላል። ወይንም እውነተኛውን ድርጊት መልኩን ሳይለውጥ ለታሪክ ያቆያል። ከዚህ አልፎ ተርፎም ፈጽሞ በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ ያልነበረና ወደ ፊትም ሊሆን ይችላል ተብሎ ባልታመነ ሁኔታ ላይ ጽሑፉን በመመስረት ለማጫወትም ሆነ ለማስደነቅ እንዳሻው ያደርጋል። በዚህ አንጻርም ሌላ ልዩ ልዩ ዓይነት የአጻጻፍ ዘይቤ መኖሩ አይካድም።
ግን ያልተፈጸመን ድርጊት ከአንዳንድ ሁኔታዎች ጋር አዳቅሎ በዚያ ላይ ተራራ የሚያህል ውሸት ቆልሎ ትናንት በሰው ሕይወት ላይ የደረሰ እውነተኛ ታሪክ ነው ማለት በስነ ጽሑፍ ላይ እንደመሸፈት ይቆጠራል። ራስን አሞኝቶ ሌሎችን ማታለል ከአንድ የብዕር ሰው የማይጠበቅ አሳፋሪ ድርጊት ይሆናል። በተለይም በአሁኑ ጊዜ አወናባጆችን ለማጥፋት ታላቅ ዘመቻ በሚካሄድበት ወቅት የግል ጥቅምን ብቻ በማተኰር ወገንን እንደጅል መቁጠር የዋህነት ይመስላል። ከእንግዲህ ወዲያ አንባቢው ሕዝብ ለብዙ ጊዜ የሚሞኝ ባይመስልም ቅሉ በድርሰት ስም ሊበዘብዙት የተነሱትን አደናጋሪዎች የስነጽሑፍ ምርመራ ክፍላችን በጥብቅ ሊቆጣጠራቸው ይገባል። ድርሰት ያለ ኃላፊነት የሚንቀሳቀስ መንኰራኩር አለመሆኑንም ጭምር ማሳመን ይኖርበታል። አለበለዚያ ውሸታሙ እንደአሸን ይፈላል።
አንባቢውም እንዲህ ዓይነቱን ሕገወጥ ድርጊት በቸልታ እንዳያልፈው ካሳሰብኩ በኋላ ለጽሁፌ መነሻ ወደሆነው ፍሬ ነገር ተመልሼ “የሚያቃጥል ፍቅር” በሚል ርዕስ የቀረበው መጽሐፍ ላይ አተኩራለሁ፣ የዚህ መጽሐፍ ባለታሪክ የሆነችው አንዲት ኢትዮጵያዊት (ዶክተር) ሐኪም ነች። አቅራቢው ወይንም ደራሲው እንበል ታሪኩ እውነተኛ መሆኑን ለማሳመን ራሷ የጻፈችው ነው ብለው በገጽ (14-15) የሚገኘውን ደብዳቤ አሳትመዋል። ተጨማሪ ድጋፍ እንዲሆናቸውም የፍቅረኛዋን ደብዳቤ በገጽ (16 - 17) ላይ አክለውበታል። ወደ ውስጥ ሳንገባ ይህን በመመልከት ብቻ የዚችን የተማረች ሴት እውነተኛ የሕይወት ታሪክ ለማንበብ እንጓጓለን። በሕመም የሚሰቃዩ ወገኖቿን ከመርዳት ይልቅ ወደ ዝሙት ዓለም የኰበለለችበትን መሠረተ ምክንያት ለማወቅ እንናፍቃለን። በዚህ ስሜት ተንደርድረን ፍሬ ነገሩን ስንዳስስ ብዙ የሚያስተዛዝቡ ድርጊቶች ያጋጥሙናል። መቼም ሁሉንም መጥቀስ ባንችልም ጥቂቶቹን ሳንጠቁም አናልፍም።
ዶክተር እግረ ፀሐይ (ስሟ ነው) የረቂቁን ሸኚ ደብዳቤ ለደራሲው የጻፈችው በሰኔ ወር ፲፱፻፷፪ ዓ.ም. ሲሆን፣ ከመጽሐፉም ለመረዳት እንደሚቻለው ድርጊቱ የሆነው ከ፲፱፻፶ እስከ ፲፱፻፷ ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ መሆኑ አያጠራጥርም። ስለዚህ ዶክተር እግረ ፀሐይ ወደ ሀገሯ የተመለሰችው ከላይ በተጠቀሰው በአንደኛው ዓመት ውስጥ ሆኖ ሳለ ገጽ 62 "......ከኢጣሊያ ሀገር በእንግሊዝ አየር መንገድ ተሳፍሬ ሀገሬ ገባሁ ........" ትላለች። በዚያን ጊዜ ደግሞ የብርቲሽ አየር መንገድ ወደ ኢትዮጵያ መንገደኞች ማጓጓዝ የሚያስ ችል ስምምነት እንዳልነበረው ስንገነዘብ፣ የዶክተሯም ታሪክ እውነተኛነቱን መጠራጠር እንጀምራለን። ይህን ጊዜ ወደኋላ መለስ ብለን በገጽ 51 ላይ የዶክተር እግረ ፀሐይ ምስል ነው ተብሎ የታተመውን ፎቶግራፍ ትኩር ብለን ስናይ ኢትዮጵያዊት መሆኗ ቀርቶ የባሕር ማዶ ሴት መሆኗ ሲከሰትልን የታሪኩም ሚዛን ወደ ውሸት ማዘንበሉን እንረዳለን። ከዚህ ላይ ደራሲው ኢትዮጵያዊ ደም ግባትንና ገፀባህርይ ለማሳየት አድማስ ተጋፍተው፣ ባህር ተሻግረው የፈረንጅ ወይዘሮን ውበት ለመዋስ የገፋፋቸው ኃይል ምን እንደሆነ ለመረዳት እንቸገራለን።
በሁለተኛው ምዕራፍ በገጽ 65 ዶክተር እግረፀሐይ በራስ መኰንን ሆስፒታል መቀጠሯን ብትገልፅም ከ፲፱፻፷ ዓ.ም. በፊት ኢትዮጵያዊት ዶክተር በዚያ ሐኪም ቤት ያለማገልገሏን ለማወቅ የጤና ጥበቃን መዝገብ ቤት መጐብኘት አያሻንም። ምክንያቱም በዚያን ዘመን በሕክምና ሞያ የዶክትሬት ማዕረግ ያገኙ አንዲት ኢትዮጵያዊት እመቤት ብቻ መሆናቸውን ስለምናውቅ ነው። እንግዲህ የዶክተር እግረ ፀሐይ እውነተኛ የሕይወት ታሪክ ነው ተብሎ የቀረበልን ጽሑፍ አንባቢን ማደናገሪያና የግል ጥቅም ሰቀቀን መወጫ መሆኑን ተረድተን አዝነን እንቀመጣለን። መጽሐፉ በኢጣልያኖች ቋንቋ ሰኰንዶ ሚስቶ እንደሚሉት ዓይነት ከርዕሱ ውጭ ይበልጡን ቦታ የሰጠው ስለ ውጭ ፖለቲካ ስለሕክምና ስለሴተኛ አዳሪዎች የጤንነት መመሪያ ሲሆን ደራሲው እግረመንገዳቸውን ተራማጅነታቸውን ለማብሰር ያህል የወደቀውን የአስተዳደር ዘይቤ ጐነታትለዋል። ይኸም ባልከፋ ነበር፣ ዳሩ ግን ደራሲው የተነሱበትን ዓላማ በመሳት አሰስ ገሰሱን በማግበስበስ የጥራዙን መዳጐስ ብቻ ቅድሚያ የሰጡት ይመስላል።
ወደ ታሪኩ እንመለስና ዶክተር እግረ ፀሐይ ከሻምበል ተፈራ ሰለሞን ጋር እንዴት እንደተዋወቁ እንመለከታለን። ዶክተሯ ሻምበሉን ያየችው የጤንነት ትምህርት በምትሰጥበት ወቅት ሲሆን እንዳየችው በፍቅር መማረኳን አልደበቀችም። እንግዲህ በዚያች ዕለት የነበረውን ድራማ በራሷ ቋንቋ ስትተርክ እንስማ። (ገጽ 86 ይመልከቱ) "...በዚህ ወቅት ከአጠገቤ ካለው ሰው ጋር እጅግ ክፉኛ በፍቅር በመያዜ ......እንግዶቹን አሰናብቼ ወደ ቢሮዬ ተመለስኩ። ያው ሰው በራፍ አንኳክቶ ገባ።"
"ዶክተር ምነው አመመዎት መሰለኝ?" ሲል ጠየቀኝ ።
“የለም ደኅና ነኝ”
“ያልገባኝን አንዳንድ ጥያቄ በቢሮዎ ልጠይቅዎት እችላለሁ?”
“አዎን”
“ይቅርታ በመጀመሪያ ብንተዋወቅ አይሻልም? ሻምበል ተፈራ ሰለሞን እባላለሁ”
“ዶክተር እግረፀሐይ እባላለሁ የኔ ወንድም ባልሳሳት የማውቅህ ይመስለኛል" ስል ውሸቴን ጠየኩት
“እንጃ አይመስለኝም" ሲል ሰውነቱን ቆጣ አድርጐ ሳቅ አለ
“አይሆንም እውጭ አገር በትክክል አውቅሃለሁ”
"እስከ ዛሬ ከአገሬ ወጥቼ አላውቅምና ተሳስተሻል ዶክተር”
ይህን ሲለኝ ክፉኛ ወሽመጤን ቆረጠው በዚህም ወቅት ከድንጋጤ የተነሳ “አግብተሀል አልኩት”
“አዎን ካገባሁ 7 ዓመቴ ነው” አለኝ
“እግዚአብሔር ግፉን ያስቆጥረውና” ትላለች ።
በዚህ ሁኔታ የሀሳብ መለዋወጥ ንግግር ቢቀጥልም እጅ እጅ እንዳይለን እዚህ ላይ እንገታዋለን። ይህ እንግዲህ ከዓማኑኤል ያመለጡ ንኰች የሚነጋገሩበት ቋንቋ ካልሆነ በስተቀር ሁለት የማይተዋወቁ በፍቅር የሚፈላለጉ ሙሁራኖች የሚጠቀሙበት የመግባቢያ ስልት ባይመስለንም ፤ ያም ሆነ ይህ እንዲህ ሆኖ ፍቅር ተመሰረተ እንባላለን።
እስከ ገጽ 93 የሚዘልቀውን የሁለቱን ወጣቶች ዲያሎግ ስንመለከት የደራሲውን የአእምሮ ጤንነት እንጠራጠራለን። በስነጽሁፍ ጉስቁልና ደረት ጥለን እየየ የምንለው ግን የብዕሩ ሰው የሀኪም ምክር ለመጠየቅ ወደ ቢሮ የገባው የጦሩ መኰንን (እብድ አለመሆኑ ተገልጾልናል) የሰው ሰው ያውም ያለመዳት ሴት ሆስፒታል ውስጥ አንቆ ግብ ግብ ገጠመ ብለው ሲያውጁ ነው። በዚህ ላይ ነው የደራሲውን የማሰብ ችሎታ የምታዘበው። በዚህ ቅጥ ባጣ ስርዓት የተጀመረው የዶክተር እግረፀሐይና የሻምበል ተፈራ ወዝ የሌለው ፍቅር በሱ ሞት ያከትማል።
የሻምበሉን አሟሟት እስቲ እንመልከት። ሻምበል ተፈራ ሰሎሞን ከጐረቤት ሀገር ጋር በነበረን የወሰን ግጭት በ1955 ዓ.ም. ጠረፋችን ለማስከበር ይታዘዛል። (ትዕዛዙ የደረሰው ከለሊቱ ሰባት ሰዓት ገደማ መሆኑን አስታውሱ) ከዚያ የጦር ልብሱን አጥልቆ ወደ አለቃው ቢሮ ይገባል። ሲወጣ ሻለቃ ይሆናል። ከጦሩ ሜዳ ጀብዱ ሠርቶ ሌተና ኰሎኔል ይሾማል። በዚህ ስንደነቅ ይሞትና አስከሬኑ ብርጋዴር ጀኔራል ይሆንላችኋል ። የቀብሩም ስነስርዓት በሙሉ ጀነራልነት ይፈጸማል። ገጽ 122 ይመልከቱ። በመሠረቱ በዚያ መጠነኛ የወሰን ግጭት እንዲህ ዓይነት የተንዛዛ የማዕረግ ዕድገት አለመሰጠቱን የመከላከያ ሚኒስቴር ዶክሜንት እናገላብጥም ፤ ይህን የመሰለ ጆሮ የሚቧጥጥ ውሸት ለማቃናት በቦታው የነበሩትን አናፈላልግም።
እንዲህ ሆኖ የሁለቱ የፍቅር ጉዞ ያበቃና የዶክተር እግረፀሐይ ሁለተኛው የሕይወት ታሪኳ ድራማ ይጀምራል። ዶክተሯ ወደ ሴተኛ አዳሪነት ለመሰማራት ያበቃት መሠረተ ምክንያት (ወደ ዝርዝር ጉዳዩ ሳንገባ) አባቷ ሊገሏት ስለፈለጉ ብቻ ነው። ይህ ደግሞ አንድን የተማረች ባለሙያ ሴት ከሐረርጌ አስደንብሮ ውቤ በረሃ የሚያሸጉጣት በቂ ምክንያት ሆኖ አይታየንም። ደራሲው ይበቃል ካሉም ይሁን ብለን የሴተኛ አዳሪነት ኑሮዋን እንከታተላለን። ዶክተር እግረፀሐይ ወ/ሮ አስናቀች ዳንስ ቤት አዲሱን ኑሮዋን ባሻሻጭነት ትጀምራለች። ሥራውን የመረጠችውም ከሐረርጌ አዲስ አበባ እንደመጣች በህክምና ሞያዋ ለመሠማራት ጠይቃ በቢሮክራሲው ብስጭትና የባለሥልጣኖችን የፍትወት ፍላጐት ለማርካት ፈቃደኛ ሳትሆን በመቅረቷ መሆኑን ትገልጻለች።
ትሻልን ፈትቼ ትብስን አገባሁ እንደሚለው የአንድና የሁለት ሹሞች ፈቃድ ለመፈጸም አሻፈረኝ ያለችው ሴት የብዙዎች አሻንጉሊት መሆንን ወደደች ብለን እንታዘባታለን። በሌላ በኩል ደግሞ ደራሲው የቀድሞውን ያስተዳደር በደል ለመግለጽ እንደ ማስረጃ ያቀረቡት የዶክተሯ እሮሮ አንካሳ ይሆንብናል። እርግጥ የወደቀው መንግሥት ያልፈፀመው ግፍ አለ ባንልም ቅሉ በዶክትሬት ማዕረግ በሕክምና ጥበብ ያውም ከምዕራብ ክልል ተመርቃ የመጣች እመቤት በዚያን ጊዜ ወዳጅ ዘመድ በማጣቷ ሥራ አልባ ሆነች ብንል ህሊና ያለው ሰው ይስቅብናል።
ዶክተር እግረ ፀሐይ እንደማንኛቸውም ሴትኛ አዳሪዎች በመሸታው ዓለም ብዙ ነገሮች ቢያጋጥማትም በገጽ 139 እንደምንመለከተው ላዳር የወሰዳት ሰው ከሰብአዊ ርህራሄ ውጭ ያን ያህል የጭካኔ ድርጊት አንድ ኢትዮጵያዊ ይፈጽማል ብለን እንኳን ማመን ቀርቶ ማሰቡም ይዘገንናል። በገጽ 150 ደግሞ በማዘጋጃ ቤቱ አንቡላንስ ሆስፒታል የገባችው ዶክተር እግረፀሐይ የታከመችበትን ሂሳብ መክፈል ስላቃታት ተከሳ የሁለት ወር እስራት ይፈረድባታል። ቅጣቷን ጨርሳ ከወጣች በኋላ ዕድል ፊቷን ትመልስላትና በአንድ የውጭ ሃገር ሰው ገድ ባይነት በአጭር ጊዜ ውስጥ ማርቼዲስ መኪና አሽከርካሪ ፣ ስመ ገናና ሴትኛ አዳሪ ትሆናለች። ከዚያም ወዳጅነቷን የመኳንንት ቤተሰብ ከሆነው ከልጅ ዓለማየሁ ደስታ ጋር አጠንክራ ፍቅራቸውም ስር ሰዶ በገነት ሆቴል ጋብቻቸውን ከፍ ባለ ስነ ሥርዓት ያከብራሉ። አዲስ ሕይወት አዲስ ኑሮ ይጀምራሉ። ልጅም ይጸነሳል። ሊሆን የሚችል ነውና አንገረምም። ግን ምንም ዓይነት መቃቃር ሳይፈጠር ፤ በመሀላቸውም ጥላቻ ቦታ ሳያገኝ ፤ አፍላ ፍቅራቸው ሳይበርድ መነሻውም ምን እንደሆነ በማይከሰትልን ምክንያት ሕይወቷን ታጣለች። የዶክተር እግረፀሐይ አሟሟት ከገጽ (207 - 208) በዝርዝር የተገለጠ ሲሆን ፍሬ ነገሩም እንዲህ ነው።
" ... በአልጋችን ላይም አረፍ ብለን እንጫወት ጀመረ ዓለማየሁ እጅግ ይወደኝ ነበርና ምን እንደሚያደርገኝም ይሳነው ነበር። ፍጹም ዓለማየሁ እየተለወጠ ሄደ።"
“እግረፀሐይ" አለ
“ወይ ዓለምዬ" አልኩት
“ብርቱካን አይደለሽ አልውጥሽ ፍጹም ቅድም እንዳየሁት ፊልም ከማፍቀሬ የተነሳ ምን እንደማደርግሽ ግራ ገባኝ።"
“ዓለምዬ?”
“ወዬ እግረፀሐይ”
“ያሻህን አድርግ”
በዚህን ጊዜ ዓለማየሁ አንድ የአሜሪካን ኮልት አወጣና "ልግደልሽ?" አለኝ
“አዎ ዓለማየሁ እስቲ በሕይወትና በሞት መካከል ያለውን ለውጥ እንይ?" አልኩት።
ከዚህ በኋላ እኔ አላውቅም። እግረፀሐይ ከፍቅረኛዋ በተተኰሰ ጥይት ሞተች ብለው ደራሲው የዶክተሯን ታሪክ ይደመድማሉ።
“የሚያቃጥል ፍቅር” በዚህ ሁኔታ ቢያበቃም ውሸት ተደጋግሞ ሲነገር እንደ እውነት ይቆጠራል በሚል ግምት ደራሲው ወደ ቅዱስ ዮሴፍ መካነ መቃብር ይወስዱናል። ከዚያ የሙታኖች ዓለም የሚገኘውን የብርጋዴር ጄኔራል መንግሥቱ ንዋይን ልጅ የኔነህ መንግሥቱን የመቃብር ሀውልት (ገጽ 199) ስሙም ሆነ መልኩ ቁልጭ ብሎ በሚታይ ሁኔታ ፎተግራፉን አቅርበውልናል። በዚህ አንጻር ደግሞ የዶክተር እግረፀሐይ የመታሰቢያ ሀውልት ያስጐበኙናል (ገጽ 209 ይመልከቱት) ግን ሀውልቱ ላይ ያለውን ምስልም ሆነ ጽሁፍ እንዳይታይ ሆኖ በርቀት የተነሳ ፎቶግራፍ በመሆኑ ማደናገሪያነቱ በግልጽ ይታወቃል። ግን የኔነህ መንግሥቱና የዶክተር እግረፀሐይ ታሪክ በምን ዓይነት መንገድ ሊያገናኙት እንደሞከሩ ባይገባኝም ሌሎች የመቃብር ሀውልቶች እንዳናይ ዕድል የምናጣው ግን ደራሲው የጄኔራል መንግሥቱንና የገርማሜ ንዋይን አስከሬናቸው ያረፈበትን ቦታ ለማግኘት በአዲስ አበባ የሚገኙትን ቤተክርስቲያን አዳርሰው ማጣታቸውን በኔነህ መንግሥቱ የመታሰቢያ ሀውልት ፎቶግራፍ ባለበት ገጽ ግርጌ ስለገለጹልን ነው ቢሆንም ድካማቸውን በመገንዘብ ሳናመሰግናቸው አናልፍም።
ከሙታኖች መንደር ተመልሰን በአንክሮ መጽሐፍ ውስጥ ያሉትን ፎቶዎች ስንመለከት የዶክተር እግረ ፀሐይ ምስል ናቸው ተብለው በገጽ (51 - 87 - 166) በተለያየ መልክ የቀረቡት ፎቶግራፎች የውጭ ሀገር ሴቶች በመሆናቸው ትገረሙ ይሆናል። ግን ሶስቱም የተለያዩ ሴቶች ሲሆንባችሁ ምን ትላላችሁ? እኔ ግን የሀፍረት ካባ አጠለኩ።
በመጨረሻም በመጽሐፉ ሽፋን በስተጀርባ ላይ በሕብረ ቀለም ካሸበረቀው የደራሲው ፎተግራፍ ግርጌ “የደራሲው ዲግሪዎች" በሚል መነሻ
1. ኦ ሰላም በስምሽ ስንት ግፍ ተሠራ ?
2. ሰላም ዋ ጥቁር ሆኖ መፈጠር ወንጀል ነወይ?
3. በገነት ውስጥ ያለ ሲኦል ።
ብለው ደርድረዋቸዋል። ብሔራዊው ዩኒቨርሲቲያችን “ኦ ሰላም ...” የሚል ዲግሪ አለመስጡትን የተማረው ክፍል ቢያውቀውም ቅሉ የዋሁ ሕዝብ ግን ደራሲውን ባለ ሶስት ዲግሪ አድርጐ ቢኰፍሳቸው አይፈረድበትም። መጭው ትውልድ ግን በሀገራችን “ጥቁር ሆኖ መፈጠር ወንጀል ነወይ? የሚል ዲግሪ ይሰጥ ነበርን? ብሎ የክርክር ምዕራፍ ቢከፍት አይደንቀንም። በመጨረሻም ደራሲውን የምናሳስባቸው ይህን ሁሉ ቅጀትና ውሸት ለማገናዘብ የሕሊና አንገት በማጣታቸው ብናዝንም አላዋቂ ሳሚ ምራቅ ለቅላቂ ይባላልና የምኞታቸው መሪ አቅጣጫውን እንዲቀይሩ የወንድምነት ምክራችን ለግሰን ትችቱንም ከዚህ ላይ እንገታለን።
✍️✍️✍️✍️✍️
በሂሱ ላይ ያለኝ ትንጥ የግል ምልከታ!!!!
ብዙ ዓይነት የሂስ መንገዶች ስላሉ፣ በግሌ ትኩረቱን የተፃፈው ነገር ላይ ብቻ የሚያተኩር የሂስ ዓይነት ደጋፊ ነኝ። ጋሽ ይልማም ያንኑ ነው ያደረጉት ብዬ አምናለሁ። መጽሐፉን ያላነበበው ሰው በርግጠኝነት ሃያሲው ደራሲውን እንደቀጠቀጡት እንደሚሰማው እገምታለሁ። ግን አይደለም። እንደውም ብዙ ብዙ ነገር እንዳለፉት ነው የሚሰማኝ። እሳቸው ያነሱት ሙሉ ሆኖ ስለተሰማኝ የምጨምረው ምንም የተለየ የአቀራረብ መንገድ ባይኖርም ዝምብዬ ማጠናከሪያ ግን ልጨምርላችሁ።
- ዶክተር እግረጸሐይ በ1934 ዓ.ም. ተወልዳ በ1950 ዓ.ም 23 ዓመት ሲሆናት ታገኟታላችሁ።
- በ7 በ8 አመቷ አንደኛ ክፍል ገብታ በ15 ዓመቷ ዩንቨርስቲ ተጓዥ ትሆናለች። በአራት አመቷ ቄስ ትምህርት ቤት ብትገባም እንደተባለው ሶስት አራት ክፍል ደብል ብትመታም ሂሳቡ ፍፁም ልክ አይመጣውም።
- ይህ ስራ እውነተኛ ታሪክ ሳይሆን የደራሲው የግል ፈጠራ መሆኑን የምተረዱት ወደ አሜሪካ ከመሄዷ በፊት ባቡር ላይ የምታገኛት ወይዘሮ አስካለ የተባለች ሴትዮ ትምህርትሽን ተይውና ቡና ቤት ላስቀጥርሽ እያለች ስታማልላት ነው። (ወደ አሜሪካ ለትምህርት የምትላክ ሴት እንደዛ ስትመከር አስቡት)... የደራሲው ዋነኛ ግብ ግን እግረ ጸሐይን ሴተኛ አዳሪ ማድረግ ላይ መሆኑ ካልቀረ ከወይዘሮ አስካለ ጋር ተስማምታ ብትቀር፣ ድርሰቱ ውሸት መሆኑ ባይቀር እንኳ የተሻለው ውሸት ይሆን ነበር ብዬ በብዙ አስባለሁ። ከዶክተርነት ወደ ሴተኛ አዳሪነት ከሚቀይራት ይሄ በእጅጉ የሚሻል ይመስለኛል።
- አባቷ ተኩሰው የሳቷት ሆዷ ገፍቶ እርግዝናዋ በጣም አስታውቆ ስለነበር ነው። ሆኖም አዲስ አበባ ቡና ቤት ወንዶች በቅርጿ አጃኢብ ሲሉ እናገኛቸዋለን።
- ታሪኳን ፅፋ የሰጠችው ዶክተሯ ራሷ ናት። እና የምትሞትበትንም ቀን እየፃፈች ነበር። ... ልክ ጥይቱ ሲመታት "ከዚ በኋላ እኔ አላውቅም" ትለናለች። ደራሲው ባሏን የዓለማየሁ ደስታን ደብዳቤ የጨመረው ይሄን ይሸፍንልኛል ብሎ ይመስለኛል።
ብቻ እንደዚ እንደዛ እያላቹ መጽሐፉ ይሄን መሰል እልፍ ነገር እንዳለው እንድታዩና የጋሽ ይልማ ሀብተየስን ሂስ አጠቀላለል ችሎታ እንድታደንቁ ነው የኔን የጨመርኩት እንጂ ሂሳቸው ምንም የማይወጣለት፣ ፍፁም መማሪያ የሚሆን ሂስ ነበር። እግረመንገዴን የወደቀን መንግስት መተቸት ያለና የሚኖር ቢሆንም የሳቸው ቢያንስ ሚዛኑን ላለመሳት እጅግ መጨነቁን ግን አይቼበታለሁ ማለት ግን ይኖርብኛል።
በመጨረሻ የመጽሐፉ ጀርባ ላይ የደራሲው ስራዎች "የደራሲው ድግሪዎች" ተብሎ ስለተገለፀው ነገር በወቅቱ ስለተፈጠረው የሕዝቡ ስሜት ልረዳ ባልችልም፣ ያን ያህል ግን አፍራሽ ሆኖ አልታየኝም። እንደውም እንደ አዲስ የፈጠራ አገላለፅ ነው የወሰድኩት። ሕዝቡ እንኳ በሌላ ቢረዳው ይህ የደራሲው ስህተት ሊሆን አይገባም። ጋሽ ይልማ መጽሐፉን ተረድተው የአንዳንድ ግለሰቦች አቀባበል አናዷቸው ያነሱት ይመስለኛል። እርግጠኛ መሆን ባልችልም።
በተረፈ "ቅልብጭ ያለ የተፃፈው ነገር ላይ የሚያተኩር ሂስ ምን ይመስላል?" ብባል "ይኸው ከላይ ያለው!" ነው መልሴ!!!
