ዐፈር ያነሣ ሥጋ ሂስ አስፋው ዳምጤ


✍️✍️✍️✍️✍️


ደራሲ - ሰይፉ መታፈሪያ ፍሬው

የመጽሐፉ ርዕስ - ዐፈር ያነሣ ሥጋ

ሃያሲ  - አስፋው ዳምጤ

ጽሑፉ የወጣበት ቦታ - መነን መጽሔት

ዘመን - ህዳር 1965 ..


✍️✍️✍️✍️✍️


ከሁሉ አስቀድሞ የመጽሐፊቱ አቀራረብ ማራኪና አስደሳች ነው። እሽፋኑ ፎቶ ላይ ጦር የያዘ አንድ ኢትዮጵያዊ ገጠሬ (ምናልባትም እረኛ) ልብ እሚሰልብ የሐይቅ ትርኢት ፊት ብቻውን ቆሟል። ጦሩ እንደ መቋሚያ እንጂ ለማስፈራሪያ አልተያዘም። በጠቅላላው ትዕይንቱ የፍልስፍናን ስሜት የሚቀሰቅስ ዓይነት ነውና ፡ ሽፋኑ ለመጽሐፊቱ ተስማሚ ነው። 


ቀጥሎ እማውጫው ይደረሳል። ፈጥኖ አንድ ጥያቄም አእምሮን ይገጫል፣ “ለምን ከፊት ወደኋላ?” ያሰኛል። በተለይም 'ነገር ከሥሩ ውሃ ከጥሩ' የሚልን አእምሮ። የሚለጥቀው መግቢያ ለዚህ ጥያቄ አጥጋቢ መልስ ከመስጠቱም በላይ፣ ለየት ካለ ካንድ አእምሮ ጋር መተዋወቅ መጀመሩን አንባቢውን ወዲያው ያስገነዝበዋል። የመግቢያው አጻጻፍ ባንድ ፊት ትምክህት የለሽ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ያንገት በላይ ትሁትነት የሌለበት ቀጥታ ገለጻ ነው። ከዚያ ሰተት ብለን ግጥሞቹን ወደ ማንበብ እንገባለን። 


ግጥሞቹ የተጻፉት በልዩ ልዩ አገሮች ከተሞች ባለፉት አሥራ ሰባት ዓመቶች ነው። ከሐረር እስከ አዲስ አበባ፣ ከፓሪስ እስከ አቴና፣ ከመካከለኛው ምሥራቅ እስከ ሰሜን አውሮጳ፣ ጸሐፊው ከ፲፱፻፵፯ ዓ. ም. ግድም አንሥቶ እስከ ፲፱፻፷፬ ዓ.ም ድረስ በጐበኛቸውና በነበረባቸው ሥፍራዎች፣ ከተመልካች ዓይን፣ ከአውጠንጣኝ አእምሮና ከአንቂ ልቡና የተፈጠሩ ናቸው። የአቀራረባቸው ቅደም ተከተል በማውጫው እንደሚታየውና በመግቢያው እንደሚገልጸው “ከአንቀልባ እስከ ቃሬዛ” በሚመሰለው አኳኋን ሳይሆን በተቃራኒው መንገድ ነው። ማለት፣ ካሁን ወደ ቀድሞው። የዚህን አቀራረብ ምክንያት ለመረዳት መግቢያውን ያነቧል። 


የግጥሞቹ አጻጻፍ ስልት በወል ግጥም አፉን ፈቶ ላደገ አንባቢ አዲስ ሳይሆን አይቀርም። ምክንያቱም ፣ ከ፷፬ቱ ግጥሞች ውስጥ ስድስቱ ብቻ የተለመደው የወል ግጥም የሚባለው ዓይነት ሲሆኑ፣ የቀሩት አምሳ ስምንቱ በአዲስ ስልት የተጻፉ ናቸውና ፤ ጸሐፊው የወል ግጥም መጻፉን በ፲፱፻፵፱ ዓ.ም. ግድም ያቆመ ይመስላል። የወል ግጥሞቹ እስከዚህ የሚያስደስቱኝ ሆነው አላገኘኋቸውም። በአማርኛ የወል ሥነ ግጥም ዓለም የመጀመሪያውን ደረጃ ከምሰጣቸው ከከበደ ሚካኤል የቅኔ አዝመራ ግጥሞች ጋር እነዚህን “ዐፈር ያነሣ ሥጋ” ውስጥ ያሉትን የወል ግጥሞች አእምሮዬ አነጻጽሮ ዝቅተኛ ደረጃ ሰጥቷቸዋል። በተለይም፣ “ሙዚቃም ድምፅ ነው” የተሰኘውን ግጥም ባነብ ፤ 

ድምፅ ነው ሙዚቃ የዜማ ምሥጢር 

 ከሠራ አካል ገብቶ በመላ የደም ሥር 

የሚርመሰመስ ትል በቁም የሚወር። ... 


ብዬ፣ ንባቤን ለማቆም ቃጥቶኝ ነበር። “ሙዚቃና የሚርመሰመስ ትል ምን አገናኛቸው” አልኩኝ። እቅኔ አዝመራ ውስጥ የሚገኘውን “ሙዚቃ” የሚለውን ግጥም ለማስታወስ ሞከርኩ። በኋላ መጽሐፉን አግኝቼ አነበብኩ ፤ 


ፈልቀሽ የተገኘሽ ከሹበርት ራስ፣ 

ከቤቶቨን ናላ ከሞዛርት መንፈስ፣ 

ከሾፓን ትካዜ ከያሬድ ልቡና፣ 

መዐዛ የሞላብሽ የብስጭት ቃና፣ 

ረቂቋ ድምፅ ሆይ ውቢቷ ሙዚቃ፣ 

ንጽሕት እንደ ፀሐይ ውብ እንደ ጨረቃ። 

...የትካዜ ከርቤ የብስጭት ዕጣን፣ 

የመልአኮች ቋንቋ የሱራፌል ልሣን፣ 

ቃናሽ ነፋስ ሆኖ ድምፅሽ ሠረገላ፣ 

ውሰጃት እባክሽ ነፍሴን ወደሌላ። 

... መንፈሴ ረካ። 

ግጥሙ ራሱ ሙዚቃ ነው። ዐፈር ያነሣ ሥጋ ውስጥ ስለሙዚቃ የተጻፉት ሁለት የወል ግጥሞች ከዚህ ደረጃ አልደረሱም። 


ስለሆነም ፣ የሰይፉ ስድስት የወል ግጥሞች ተሰጥኦ እንዳለው በጊዜያቸው ተንብየዋል። ትንቢታቸውም ለመድረሱ በመጽሐፉ ውስጥ ቀደም ብለን የምናነባቸው ግጥሞች ምስክሮች ናቸው። እዚህ ላይ እንደገና ለማስገንዘብ የምፈልገው፣ መጀመሪያ የተጻፉት የወል ግጥሞቹ ቢሆኑም፣ የሚገኙት ወደ መጽሐፉ መጨረሻ ነው። ስለዚህ ፣ መጽሐፉን ስናነብ አሁን ከደረሰበት ደረጃ ተነሥተን ጀማሪ ወደ ነበረበት ደረጃ መድረሳችን ነው። ይኸን ስንረዳ ፣ ጀማሪውን ገጣሚ ከአንጋፋው የወል ስነ ግጥም ባለቤት ጋር ማነጻጸሩ ትክክለኛ ፍርድ ነው ወይ? ያሰኘናል። በተለይም ፣ የተጠቀሰውን ግጥም ፣ ሰይፉ ካሁኑ ዕድሜው በአሥራ አራት ዓመታት ያንስ በነበረበት በተማሪነቱ ወቅት የጻፈው መሆኑን ስናውቅ። የወል ግጥሞቹን ዝቅ ያለ ደረጃ የሰጠኋቸው ፣ ጥቂቶች (ሰይፉም ጭምር) ከደረሱበት የኪነት ደረጃ በሚገኝ ሚዛን ስለመዘንኳቸው ነው እንጂ ፣ የአብዛኛዎቹን ገጣሚዎች ሥራዎች በምለካበት መለኪያ ብለካቸው አንሰው አላገኛቸውም፡፡ እንዲያውም ከወል ግጥሞቹ ውስጥ ይልቃል የምለው፣ “ሮማ” በወል ሥነ ግጥም ዓለም ሥፍራ ይሰጠዋል ብዬ እገምታለሁ። 


ከ፲፱፻፶ ዓ. ም. ግድም ጀምሮ የግጥሞቹ የአጻጻፍ ስልት መለወጥ ይጀምራል። ስንኞች ማጠር፣ መሥመሮች መዛነፍ ያመጣሉ። ነጥቦች አልታሰቡበት ተገኝተው ፣ አሉ እተባሉበት ይጠፋሉ። (ጸሐፊው ምክንያቱን በመግቢያው አስረድቷል።) የግጥሞቹ ድምፅ አወራረድ ወደ ንግግር ይቀርባል። ቤት መምታት ቢኖርም ከመጀመሪያ ደረጃነቱ ይወርዳል። 


ለየት ባለው ሥልት ከተጻፉት አምሳ ስምንት ግጥሞች ከሁሉም የሚረዝመው “የመተሃራው ባላባት” የተሰኘው ተራኪ ግጥም ነው። አሥራ አራት ገጽ ተኩል ነው። መተሃራን በባቡርም ሆነ በመኪና እያቋረጠ የሚመላለስ ሰው ይኸን ግጥም ካነበበ በኋላ ያን ቦታ አመለካከቱ ይለወጣል ብዬ እገምታለሁ። አተራረኩ በውበት ሳይዛነፍ ሳይረግብ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ይዘልቃል። 


...እሱን፣ እሱን፣ ያን እንጀራ፤ 

ያንን ነፍስ አንድ እንጀራ፣ 

ረጋገጡት አሉ፣ ካፈር ደባለቁት፣ 

                                      ያን ለት 

የመተሃራው ባላባት 

ያ ጡረኛ ወልደ መዓት፣ 

ልጁን የዳረ ለት።... 

እያለ ተረቱን ይጀምርና፣ 

አጀብ አጀብ አጀቡ ይገርማል፣ 

ለካን የእንጀራም ጡር እንደዚህ ይደርሳል። 

ብሎይደመድማል። በሁለቱ ጥቅሶች መካከል ያለው (ረጅም) ሥዕላዊ ገለጻ ድንቅ ነው። 


በመጽሐፊቱ ውስጥ የሚገኙት አብዛኛዎቹ ግጥሞች መካከለኛና አጫጭር ናቸው። ከአጫጭሮቹ መካከል “ሕይወት እንቆቅልሽ” የተሰኘው ነው ፣ የመጽሐፊቱን አርእስት የወለደው። ግጥሙም እነሆ፣ 

ሙዳ ሥጋዬ ወድቆብኝ፣ 

መሬት 

ዐፈር አንሥቶብኝ፣ 

እንዳልበላው አሸዋው፣ 

እንዳልተወው ሥጋው። 

 ሕይወት! ሕይወት! 

 ፍቺም የላት። 


ዝብዝብ ሳያበዛ ፣ ቃላት ሳይባክኑ ፣ ቀላል ምሳሌ በመስጠት የሕይወትን ግራ አጋቢነት ያሳያል። ሕይወት ትርጉም ብቻ ሳይሆን ፣ መላቀቂያም (መፋቺያም) ነው የሌላት። ባንድ ፊት መኖር አይቻልም ብንል በሌላ በኩል ደግሞ ላለመኖር እንቸገራለን። “ሥጋውን ልንበላውም ልንተወውም አንችልም።” 


እንደተጻፉባቸው ቦታዎች መብዛትና እየተጻፉ እንደ ተጠራቀሙበት ዘመን ርዝመት ግጥሞቹ ስለ አያሌ ልዩ ልዩ ነገሮች ናቸው። ስለ ፍቅርና ትዝታ፣ ስለ ኀዘንና ደስታ፣ ስለወንዝ፣ ስለዛፍ፣ ስለመኪና፣ ስለሕፃን ፤ ስለከዋክብት፣ ስለልደትና ሞት ... 


ስለሞት ከጻፋቸው ውስጥ በተለይ ሁለቱ ፡ (መልስ የሌለው ዋይታና ደብዳቤዬ ለምንድር መልስ አጣ) የተጻፉት ሞት ስለጠለፋቸው ሁለት ወዳጆቹ ቢሆንም ጥሩ ተዋጥተዋል። “ቢሆንም” ያልኩበት ምክንያት በዘመናችን ስለሞተ ወዳጅ ወይም ዘመድ የሚጻፉትንና የሚያጽፉበትንም ዓላማ በማስታወስ ነው። ዓላማቸው ለማሞገስ፣ ለማወደስ ስለሆነ ያልሆነውን ያልተባለውን ይቀባጥራሉ። 


እነዚህ የጠቀስኳቸው ሁለት ግጥሞች ግን ከጥልቅ ስሜት መንጭተው ያንኑ ሕያው አድርገው የሚያስቀሩ ናቸው። 


ስል ደጅ ደጁን፣ 

ስል ደጅ ደጁን፣ 

የናትና የልጁን፣ 

የሩቅ ጥሪ፣ ኡኡታ 

የተቀላቀለው ዋይታ፣ 

ረዥም ረዥም ዋይታ 

እስከ መቃብር ማዶ 

ሄዶ ሄዶ፣ 

የሙት አንጀት የሚያምታታ 

                          ሰምቼ ... 

... ታዲያ ምን ልሁነው 

እንደናትና ልጁ 

በንባ እንፋሎት የሚፈጁ 

ኡኡ አልለው። 

አልጣራው። 

ኡኡ ብለው ብጣራው፣ 

ምን ይላል ሰው ... 


በኔ ግምት ፡ የአማርኛ ልብ ወለድ ሥነ ጽሑፍን ፍቅር እስከ መቃብር ወደፊት እንዳንቀሳቀሰው፣ ዐፈር ያነሣ ሥጋ፣ ለአማርኛ ሥነ ግጥም ዕድገት መልካም አንቀሳቃሽ ነው።

ስለ ጸሐፊው/ዋ እርሶ የሚያውቁት የተለየ ነገር ካለ፣ እዚህ ሲጠቀስ የጎደለ ነገር ከተሰማዎት፣ አዲስ ተጨማሪ ስራ ሲያገኙም ኮመንት መስጫው እርሶን እየጠበቀ ነው።

Comment

Ads

advert
advert