ከአድማስ ባሻገር ሂስ ሙሉጌታ ሉሌ


✍️✍️✍️✍️✍️


ደራሲ - በዓሉ ግርማ

የመጽሐፉ ርዕስ - ከአድማስ ባሻገር

ሃያሲ  - ሙሉጌታ ሉሌ

ጽሑፉ የወጣበት ቦታ - መነን መጽሔት

ዘመን - ጥቅምት 1963 ..


✍️✍️✍️✍️✍️


ዎልተር ሊፕማን የተባለው የታወቀው አሜሪካዊ ጋዜጠኛ አንድ ጊዜ የጻፈው ቃል ትዝ ይለኛል። «ደራሲ ጋዜጠኛ መሆን የለበትም። ጋዜጠኛም ደራሲ ሊሆን አይችልም»። በዚህ በኩል የበርናርድ ሾውም አሳብ ተመሳሳይ ነበረ። በርናርድ ሾው እንደ ሊፕማን ሁሉ አንድ ደራሲ ደጋግሞ ጋዜጣ ላይ የሚጽፍ ከሆነ ከፍተኛ ዋጋ ሊኖረው የሚችል አሳብ አያቀርብም የሚል እምነት ነበረው። በአጭሩ አሳቡ ፤ የአጻጻፍ ስልቱ ፥ በጋዜጣ ላይ ባክኖአል ለማለት ነው። ወዲህም የጋዜጣ ሥነ ጽሑፍ እንደ መጽሐፍ ስለማይረቅቅ በስልቱ የረከሰ በቋንቋውም ወረድ ያለ እጅግ ሕዝባዊ ይሆናል ብሎ በመፍራት ነው። 


የእነዚህን ሁለት የታወቁ ሰዎች አሳብ ሙሉ በሙሉ ባንነቅፍም ለመደገፍ ግን አንችልም። ምክንያቱም ከጋዜጠኞች መካከል በየአገሩ ታላላቅ ደራስያን በመገኘታቸው ነው። ለምሳሌም ያህል ዎልተር ሊፕማን ራሱ የተደነቀ ደራሲ ነው። ስቱዋርት አልሶፕ ሌላው ታላቅ ደራሲ ነው። በቅርቡ የሞተው የቢቢሲው ሪቻርድ ዲንቡልቢ የታወቀ ደራሲ ነበር። « ከአድማስ ባሻገርን » ካነበብን በኋላ ደግም በዓሉ ግርማን ከዚህ ተራ ልናስወጣ አንችልም። በዓሉ ግርማ በብሔራዊው የጋዜጣ ዓለም ውስጥ ተሰልፎ በቃላት የተዋጋ ቢሆንም ፥ በመጻሕፍት ሥነ ጽሑፍም ጽሑፍም በኩል ቀላል ያልሆነ ባለሙያነቱን አስመስክሮአል። በብሔራዊው የጋዜጠኝነት መስክ ውስጥ ሩጦ እንደ ጋዜጠኛነቱ ዝቅተኛ የሆነ መጽሐፍ አላቀረበም። በጋዜጣና በመጽሔትም ላይ ተዝረክርኮ ያላለቀ አሳብ ፤ ተሟጥጦ ያልተጨረሰ የቋንቋ ሀብቱን አዲስ ዓይነትና አዲስም በሆነ መጽሐፉ አቅርቦአል። ከቶውንም በዓሉ ጋዜጠኛም ቢሆን ይበልጥ ግን የደራሲ ካባ መልበስ ያለበት መስሎአል። 


ለበዓሉ ግርማ «ከአድማስ ባሻገር» የመጀመሪያው መጽሐፍ ነው። የመጀመሪያ የሥነ ጽሑፍ ድሉም ሳይሆን አልቀረም። እንደ እውነቱም ከሆነ ለአንድ ሰው መነሻው የጠዋት ሀብቱ ካማረ የኋላውም (የማታው) የበለጠ ሊያምርለት ይችላል። ፈረንጆች ጥሩ መነሻ ግማሽ ድል ነው የሚሉት ዓይነት ነው። 


ከአድማስ ባሻገር በገጽ ብዛት መለስተኛ ውፈር (ውፍረት) ካላቸው መጻሕፍት አይበልጥም። ፻፹፮ ገጽ መለስተኛ መጽሐፍ የሚያሰኘው ነው። ግን መጽሐፉ ከሁሉ አቅጣጫ የሚነካቸው ጉዳዮች ፤ የአንዳንድ አስተሳሰቦች ጥልቀት፤ ከየአኳያው ደራሲው ሊያየው የሞከረው የቁም ነገር ጥልቀት ለአማርኛ ሥነ ጽሑፍ አንድ መጠነኛ ድርሻ መፈጸሙን ይመሰክራል። 

 * 

በቅርቡ ከቦሎኛ (ኢጣልያ) እንደ ተነገረው ፖል ቨርሌይን የተባለ ፈረንሣዊ ባለቅኔ «ወንድና ሴት» (ማን ኤንድ ውማን ) የተሰኘው የግጥሞች መጽሐፍ ጸያፍ ነው ተብሎ በዳኞች ብያኔ መሠረት ከገበያ ወጥቶአል። ደራሲውም ለአምስት ወራት እንዲታሠርና ፫፻፳ ብር መቀጫ እንዲከፍል ተፈርዶበታል። በብዙዎች ምሥራቃውያን አገሮች የ ሩካቤ ጉዳይ እንደ ነውርና እንደ ከፍተኛ ጸያፍ ጉዳይ ይቆጠራል። ስለዚህ ለምሳሌ አንድ ሕፃን « እንዴት ተወለድሁ ? ከየት ወጣሁ ? ለምን አባቴ አያረግዝም ? እናቴ ሁል ጊዜ ብቻዋን ለምን ታረግዛ ለች ? » ብሎ ቢጠይቅ ከቶውንም ጥፊ የሚያቀምሰው ወላጅ ሊኖር ይችላል።  


በጠቅላላው የሩካቤ ጉዳይ ሥርየት እንደ ሌለው ኃጢአት ይቆጠራል። ይህንን ነባርና ከመሠረቱ ግን ትክክለኛ ያልሆነ የእምነት የብረት ሰንሰለት ነው በዓሉ ግርማ በአንድ በኩል ሊሰብር የታገለው። ባህል በሚል መሸፈኛ ሥር ባለው ጥረሽ ላይ ነው ወጣቱ ደራሲ በቃላት ኃይል የዘመተው። እንደ እውነቱም ይህን ወደ ኋላ የሚጐተት ኃይለኛ ሰንሰለት ከአንገት ለማውለቅ የሚቻልበት መንገድ ማለት ይኸው ነው። 


በቅርቡ ወደ ምዕራብ ጀርመን ለጉብኝት የሄዱ ሁለት ወጣቶች አንድ ዓይነት የአጋጣሚ ልምድ አግኝተዋል። አስተናጋጃቸው የነበረች አንዲት ጀርመናዊት ወጣት ጃዝሚን የተባለ መጽሔት ገዝታ ከውስጥ ያልተከፈተውን የተጣበቀ ገጽ ከቦርሳዋ አንዲት ሴንጢ ብጤ አውጥታ ቀደደችው ። ከውስጥ የነበረው የሩካቤ ሥጋ ትርእይት ልዩ ዓይነት ነበር። በዚህን ጊዜ በንጹሕ የኢትዮጵያዊነት የጨዋነት ስሜት ወዲህም የአ ውሮፓዊቱን ሴት የሴትነት የኀፍረት መንፈስ ለመጋራት በማሰብ ወጣቱ « አይ ይኸ ብልግና ነው ። ዚስ ኢዝ ደርቲ » አለ። በዚህን ጊዜ አውሮፓዊቱ ሴት እጅግ ተቆጣች። « ይህ ነገር መጥፎ ነው ካላችሁ አንቺ መጥፎ ነሽ ማለታችሁ ነው » ብላ ተቀየመች። የቦሎኛውን ምሳሌ ያመጣነው በአንዳንድ ክፍለ ዓለም ያለውን የሩካቤ ስውርነትና ከፍተኛ የምስጢራዊነት እምነት ለማመልከት ነው። ጀርመናዊቱ ሴት ግን ሩካቤ ግልጽ ተግባር ፤ ምግብ እንደመመገብ ያለ የተፈጥሮ ግዴታ ፤ ባዮሎጂካዊ ፍላጐት ነው የሚለውን ዘመናዊ አስተሳሰብ የያዘች ናት። ባል አገባሁ እንዳትል አንድ በርሜል ላብ እንደምትደፍቅ የአገራችን ወጣት ሴት ዓይነት አይደለችም። 


በአጭሩ ለመግለጥ ያህልም በዓሉ ግርማ በ« ከአድማስ ባሻገር » መጽሐፉ አንድ የሞከረው ትልቅ ጉዳይ አለ። ይኸውም ሩካቤ መብራት ጠፍቶ በጨለማ ተከልለው የሚያወሩትና የሚፈጽሙት ተግባር ብቻ አለመሆኑን አስረድቶአል። በዓሉ ሁለት የሚዋደዱ ወጣቶች ኑሮአቸውን ራሳቸው በሚፈልጉት መንገድ እንዳይመሩ የሚያጋጥማቸውን ትግል ፡ ሳይቀር አብራርቶአል። ፍቅረኞች የራሳቸውን የፍቅር ዓለም መሥርተው ፡ የግላቸው የሆነ የፍቅር ግንብ ቀጥረው ፤ የብቻቸውን የፍቅር ድንኳን ተክለው እንዳይኖሩ ከሦስተኛ እጅ የሚመጣውን ጣልቃ ገብነትም ሳይቀር አመልክቶአል። የሌሎች ሰዎችን ጣልቃ ገብነት በዓሉ ራሱ የሚያየው ለእነሱ ባልተፈጠረ የፍቅር ዓለም ውስጥ ገብተው የኑሮን ሥዕል እንደሚያበላሹ ነው። 


ከዚህም በላይ በሁለት ትውልዶች መካከል ያለው የአስተሳሰብ ልዩነት በግልጽና በሚገባ ተወስቶአል። ለሥራና ለእድገት በማሰፍሰፍ ላይ ያለው የዘመኑ ትውልድ የሚመለከተው ወደፊት ነው። ሌላው ትውልድ ደግሞ ወደ ኋላ የቀረውን በዝምታ ዓለም ውስጥ ያረፈውን ትውልድ መኩሪያና መመኪያ አድርጎ ይመጻደቃል። በመቃብር ዓለም ውስጥ ያረፈውን በድን አካል ወደ ሕልው መልሶ በቃላት ኃይል ትንሣኤ ሙታን ያፈጥንለታል ። « ስለ አባት ስለ አያቶች ብቻ የሚያወራ ሰው እንደ ድንች ነው የእሱ መልካም ፍሬ ከመሬት በታች ነውና » የሚለውን አነጋገር በትክክል ለማሳየት አባተና እናቱን የበዓሉ ብርዕ ፈጥሮአቸዋል። 


ለበዓሉ ግርማ «ከአድማስ ባሻገር» የመጀመሪያ መጽሐፍ ቢሆንም ፡ በአጻጻፉ ስልት የታወቁ ደራስያንን ከአሁኑ ይመስላል። የጠባያት አመራረጡ ፥ የታሪክ አጽም አመሠራረቱ ፥ የአንባቢን አሳብ የማባከኑና ልብ የማቆሙ ስልትና በጠቅላላውም ዘይቤው የታወቀውን እንግሊዛዊ ጸሐፊ ሰር ራይደር ሐጋርድን አስመስሎታል። በተለይ በአንድ መጽሐፍ ውስጥ የተደጋገሙ ትራጂክ ሁኔታዎች መፍጠሩ የበለጠ ከሐጋርድ ጋር ያመሳስለዋል ። አበራ በወህኒ ቤት ሲማቅቅ ወንድሙ አቶ አባተ ሉሊትን በኃይለ ማርያም ጠርጥሮ ኃይለ ማርያምን ገደለው። እዚህ ላይ በዓሉ ጥንቁቅ ደራሲ ነበር። ሉሊትን ከመድረኩ አላሰናበታትም። አልገደላትም። እንደ መጽሐፉ አቀራረብ ኃይለ ማርያም የሞተው ወዲያው ነው። ጠበቃው ተስፋዬም የሩቅ ጓደኛው ነው። ይሁንና የኑዛዜውን ቃል ለአበራ የወሰደለት ጠበቃው ነው። በመጽሐፉ ውስጥ በዓሉ በቀጭን ክር ሊያይዘው ይችል የነበረው ተስፋዬ እንዴት እንደ ደረሰና እንዳገኘው በመግለጽ ነበረ። አላደረገም። 


የኢትዮጵያ ራዲዮው ጸጋዬ ደባልቄ በዛሬዪቱ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ላይ የበዓሉን «ከአድማስ ባሻገር» ሲተች በዓሉ ቃላት አያባክንም ብሎ ነበር። በዚህስ አልስማማም ። በዓሉ ማባከን ብቻ ሳይሆን ቃላት ይዘራልም። በዚህ የተነሣ ቃላት ደራርቦ ደራርቦና ጉንጉኖ አቅርቦአል። የቋንቋን በኢኮኖሚ መያዝ አይቀበልም። የበዓሉ አሳብ በቋንቋ ውበት ላይ እያረፈ—ሰውዬውም በውበት ያምናል—የአንድ ዘር ቃላትን ማሳሳት (ቶቶሎጂ) አሳይቶአል። 

ለምሳሌ « የኑሮው ሕልውና » 

« በውበትዋ ማማር የምትኮራ» ይላል። በዓሉ አያውቀውም ለማለት ሳይሆን ሕልውናም ማለት ኑሮ ማለት ነው። ውበትም ማማር ነው። ከዚህም በቀር በየገጹ አንዳንድ ያልተለመዱ አገላለጦች ይገኛሉ። የቋንቋን ሥርዓት ጥሶ የትርጓሜን ገደብ አልፎ ውበትን ለመግለጥ ያለውን ጭንቀት ተወጥቶታል። ለምሣሌ እም ኀበ አልቦ ማለት ከምንም ከዜሮ (From nothing) ማለት ነው። ዓይነ ቁራኛው ናት ይላል በሌላ ሥፍራ። የዓይን ፍቅረኛው ናት ለማለት ነው። ዓይነ ቁራኛ ማለት ግን እንዲያ ማለት አይደለም። 


እንደ ክቡር አቶ ሐዲስ ዓለማየሁ መጽሐፍ ሁሉ የሚነካካው የኅብረተሰብ ኑሮ ውዝግብ እጅግ በዛ ያለ ነው። እንደ ፍቅር እስከ መቃብርም በሁለት ወጣቶች ፍቅር መካከል በአገራችን ያለውን የወላጆች ጣልቃ ገብነት የአጥንት ኩራትና እምነት ያብራራል። የትውልድን ግጭት መነሾ ባልታወቀ ሁኔታ አቅርቦአል። ከአድማስ ባሻገር ያለው ሕልውናም ተቀባይነት ያጣ ሥርዓቱ ድል ሲደረግ ነው። «ከአድማስ ባሻገር» ያለ ኑሮም የሚሰምር በሳይንቲፊካዊ አስተሳሰብ ሲደረስ ነው። 


ደራሲው እንደ አቶ ሐዲስ ሁሉ የሆሄያትን ብዛት አይደግፍም። አዳጋሚ ሆሄ ያላቸውን እንደ ሐ ዓ ያሉትን ሁሉ ገድሎአቸዋል። ግን አዳጋሚ ድምፅ ባላቸው(ዲፍቶንግስ) አልፈረደባቸውም። እንደ አቶ ሐዲስ ሁሉ ኋ ፥ ሏ ፥ ሯ ፡ — ፡ ወዘተ ያሉትን በዝርዝር ሁዋ ፡ ሉዋ ፡ ሩዋ ፡ ሙዋ በማለት አልተጠቀመባቸውም። ቢሆንም ሆሄያትን በማሻሻል ረገድ አንድ ሌላ ርምጃ ወስዶአል። 


የበዓሉ አንድ ዘይቤና የሐረግ አመሠራረት ሁኔታ ደግሞ ከመጽሐፉ ውስጥ በጉልህ ይታያል። ይኸውም በአጻጻፍ ስልቱ በዓሉ ተምሳሊቶችን ማብዛቱ ነው። በየገጹ በርከት ያሉ ተምሳሊቶች (በእንግሊዝኛው ሲሚሊ) ያበዛል። «ከአድማስ ባሻገር» ሌላው ውበቱ በሽፋኑ በኩል የተደረገው ብርቅ ሥዕል ነው። ይኸ ራሱ በጽሑፋችን ታሪክ ውስጥ አንድ ራሱን የቻለ መጠነኛ እንቅስቃሴ ነው። ዳሩ ግን የመጽሐፉ አርእስት—«ከአድማስ ባሻገር» (-ቤዮንድ ዘ ሆራይዘን) በፈንረጅም አላነበብሁትም እንጂ ያለ ይመስለኛል ። አጋጣሚ ነው እንበል። ቢሆንም በዓሉ ከአድማስ ወዲያ ማዶና ከአድማስ ወዲህ እንዲህ ያለውን ኑሮ ለማገናኘት ሞክሮአል። በነገና በዛሬ መካከል ሁነኛ መሸጋገሪያ ድልድይ ለማቆም ጥሮአል። ይህም መጽሐፉ በእርግጥ ሰሞኑን ከሚነበቡ መጻሕፍት ተራ ውስጥ የሚገባ ነው።

ስለ ጸሐፊው/ዋ እርሶ የሚያውቁት የተለየ ነገር ካለ፣ እዚህ ሲጠቀስ የጎደለ ነገር ከተሰማዎት፣ አዲስ ተጨማሪ ስራ ሲያገኙም ኮመንት መስጫው እርሶን እየጠበቀ ነው።

Comment

Ads

advert
advert