✍️✍️✍️✍️✍️
ደራሲ - ደጃዝማች ከበደ ተሰማ
የመጽሐፉ ርዕስ - የታሪክ ማስታወሻ
ሃያሲ - አቤ ጉበኛ
ጽሑፉ የወጣበት ቦታ - የዛሬዪቱ ኢትዮጵያ ጋዜጣ
ዘመን - ሰኔ 1962 ዓ.ም.
✍️✍️✍️✍️✍️
የታሪክ ማስታወሻ በሚል ርእስ በክቡር ደጃዝማች ከበደ ተሰማ የተጻፈውንና የመጽሐፉ ሽያጭ ገቢ ለወ.ወ.ክ.ማ እንዲሆን ተሰጥቶ የታተመውን መጽሐፍ በ፲ (አሥር ብር) ገዝቼ ከጀመርሁበት ጊዜ ጀምሮ በመካከሉ ሌላ መጽሐፍ ጣልቃ ሳላገባ ከሙሉ ስሜት ጋር በአጭር ጊዜ አንብቤ ጨርሼዋለሁ።
መጽሐፉን እንዳገኘሁት ለመግዛትም ሆነ በአጭር ጊዜ ከሙሉ ስሜት ጋር አንብቤ ለመጨረስ የገፋፋኝ ምክንያት ከአምስት መቶ ገጽ በላይ ሆኖ በጥሩ ወረቀትና ከፍተኛ በሆነ ጥራዝ አምሮ መቅረቡ አይደለም። ወይንም የስሙ አጠራር አይደለም። እንዳጋጣሚ ገለጥ አድርጌ በተመለከትሁት ገጽ ላይ ያገኘሁት ነገር መጽሐፉን ከጄ እንዳላወጣው አስገደደኝ።
ታሪክ በሀገራችን ከጥንት ጀምሮ ሲጻፍ ኑሯል። አሁንም ይጻፋል። ወደ ፊትም ይቀጥላል። እስከ ዛሬ የታሪክ ማስታወሻን የመሰለ ታሪክ ሲቀርብልን ግን ፤ (ምናልባት ተሳስቼ ቢሆን እንደ ግል አስተያየት አድርጋችሁ ይቅርታ አድርጉልኝ) የመጀመሪያ ጊዜ ነው። ይህን ያልሁባቸው ምክንያቶችም አንደኛ ደራሲው ክቡር ደጃዝማች ከበደ ተሰማ እጅግ ውብና ታማኝ በሆነው መጽሐፋቸው የገለጿቸው ሁኔታዎች ሁሉ ራሳቸው በቀጥታ ተካፋይ የሆኑባቸው ናቸው።
፪ኛ እኒህ በጦርም በፖለቲካም ሁኔታዎችና አጋጣሚዎች በታሪኩ ውስጥ ካሉት አንዳንድ ሰዎች ጋር ግጭት ሳያጋጥማቸው እንዳልቀረ የማያጠራጥሩ አዛውንት መኰንን ጠላቶቻቸው እነማን ወዳጆቻቸው እነማን መሆናቸውን እንኳ ለመለየት በሚያስቸግር ትክክለኛ ምስክርነት እገሌ ወዳጄ ስለሆነ ያለአግባብ ላሞግሰው እገሌ ጠላቴ ስለሆነ ለሙያው የሚገባውን ምስጋና ልንፈገው ሳይሉ በመሥራት ታሪክን መርምሮና አጥንቶ ለትውልድ ማስተላለፍ ዋነኛውና ቋሚው ሥራችን ነው የሚሉ የታሪክ ሊቃውንት ብዙ ጊዜ አንድ ዓይና እየሆኑ ለተገኙበት ስሕተት ሳይንበረከኩ ተገኝተዋል።
፫ኛ በአጻጻፉ ላይ የሚታየው የቋንቋና የሐሳብ ግልጽነት ደራሲው ዕድሜያቸው ለዕውቀትና ለማስታወስ ካስቻላቸው ጊዜ ጀምሮ ስለሀገራቸው ጠቅላላ ወግና ባህል እንዲሁም የፖሊቲካና የጦር ሁኔታ የተረዱትን ቀጥ ባለመንገድ ለመግለጽ መቻል፤ መጽሐፉን ለማንኛውም አንባቢ ምቹ አድርጎታል።
በታሪክ ማስታወሻ ውስጥ አንዱን ለማሞገስ ሌላውን ማኳሰስ በፍጹም የለም። ደራሲው ደግ ከሚባልም ሆነ ክፉ ከሚባል ሰው ያዩትንና የሰሙትን በቀጥታ ከመግለጽ በቀር ማንንም በትችት ሲክቡ የማንንም ሐሳብና ሥራ በትችት ሲንዱ አይታይም። ደራሲው ለሀገሩ የሚጠቅም ሥራ ሲሠራ ያዩት ሰው ሁሉ ጥሩ ኢትዮጵያዊ ሁኖ ቀርቧል። ክፉ ሲሠራ ያዩትንም ያው የሠራውን ለአንባቢ ከማቅረብ በቀር በስሜት የተመራ ብዙ የግል ፍርድና ትችት ሊሰጡበት አልቃጡም። ምናልባት ደራሲው በሕይወት ዘመናቸወ ውስጥ ያዩት ክፉና ደግ ነገር ያስተማራቸው ትምህርት ይህን ከብዙ ሰው ላይ ሊታይ ያልቻለ ትምህርት ሰጥቶአቸው ይሆናል። ወይም የተፈጥሮ ሚዛናዊነት ሊሆን ይችላል።
የታሪክ ማስታወሻ የያዘው ታሪክ ደራሲው ነፍስ ካወቁበት ጊዜ ጀምሮ ፋሽስት ከኢትዮጵያ ተባሮ የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት መልሶ እስከተቋቋመበት ባለው ጊዜ ውስጥ ራሳቸው ተካፋይና ተመልካች ሁነው ያዩትን ነው። ስለዚህ የረጅም ዘመናት ታሪክ አይደለም። የአንድ በዕድሜ የታደለ ሰው ዕድሜ ያህል ረጅም ጊዜ ያለው ታሪክ እንኳ አይደለም። ነገር ግን በውስጡ ባለው ግልጽ ያለ አድልዎና ውሸት ያላጠቃው ገለጻ ብዙ ብዙ ነገሮች ሊያስተምረን የሚችል ነው።
በዚህ የአጭር ጊዜ ታሪክ ውስጥ ከምንማራቸው ዋና ዋና ነገሮች መካከል
፩ኛ የመሸጋገሪያ ዘመን ችግር የሚባለው ነገር ቀደም ሲል መጀመሩ።
፪ኛ ምንም እንኳ የታሪኩ ጊዜ አጭር ቢሆን ያለፉት ኢትዮጵያውያንን የኑሮ ፍልስፍና መግለጹ ፤(ሴራው ተንኮሉ ሰብቁ እንጀራ ፍለጋው ክህደቱ መለያየቱ ፤ በዚሁም ጐን ታማኝነቱ፤ የሃይማኖቱ ጥብቀት ፤ የሀገር ፍቅሩ፤ ወኔው ፤ ጀግንነቱ ፤ ይሉኝታው ፤ ትዕግሥቱ በጠቅላላው እንደማንኛውም አገር ሕዝብ የኢትዮጵያ ሕዝብም መላእክት ወይም ሰይጣናት ሳይሆኑ የሰውነት ትልቅነትም ትንሽነትም ያለበት የሰውነት ባሕርይ የነበራቸው ሰዎች እንደነበሩ አሁንም እንደሆኑ ይገልጻል ። )
፫ኛ/ ደራሲው በራሳቸው መንገድም ሆነ በሌላ መንገድ የኢትዮጵያንና የኢትዮጵያውያንን ታሪክ ለሚጽፉ ሰዎችም ታላቅ ትምህርትና ምሳሌ መሆኑ ደራሲው በቤተ መንግሥት ክፍል ያደጉና ከሹመት ወደሹመት ሲራመዱ የኖሩ ቢሆኑም በጽሑፋቸው ለግርማዊት ንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱ ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ፍጹም ታማኝ የሆኑትን ያህል በየመልኩና በየቦታው ለተራው መኰንን ለተራው ኢትዮጵያዊ አርበኛ የሚመሰገንበት ምክንያት ካለ ለማንኛውም ተራ ሰው በኢትዮጵያዊነታቸው ፍጹም ታማኝነት አሳይተዋል። ከአንድ ታላቅ ኢትዮጵያዊ የሚፈለገውና የሚጠበቀው ተግባር ይህ ዓይነቱ ይመስለኛል።
ይህ መጽሐፍ ጥሩና ግልጽ በሆነ ቋንቋ ቢጻፍም እንደብዙ የታሪክ መጻሕፍት ሁሉ በታሪክነቱ የሥነ ጽሑፍ ዘርፍ መሆኑ ባያጠራጥርም የእኔን ልብ የመታኝ ግን በሥነ ጽሑፍነቱ ሳይሆን በእውነተኛነቱና በታማኝነቱ ነው።
ክቡር ደጃዝማች ከበደ ተሰማን የማውቃቸው አካላቸውን በፎቶግራፎች መንፈሳቸውን በአንዳንድ ጽሑፎች አማካይነት ብቻ ነበር። በታሪክ ማስታወሻ አማካይነት ግን ቢቀር ቢቀር ከመንፈሳቸው በመቶ ሰባ አምስቱን ያህል ለመረዳት የቻልሁ ስለመሰለኝ አገራችን እርሳቸውን የመሳሰሉ ኢትዮጵያውያን እንደነበሯትና እንዳሏት ያለምንም ጥርጣሬ እንዳምን አድርጎኛል።
ይህ የምንመካበት ፤ ልንመካበትም የሚገባው ከሦስት ሽህ ዓመታት በላይ ዕድሜ ያለው ነፃነት በከንቱና በተረት እንዳልቆየ ቅርብ የሆነውን የትናንትና ሁኔታ ብቻ የሚገልጽልን «የታሪክ ማስታወሻ» ታላቅ ምስክር ነው።
በዚህ መጽሐፍ ላይ በኔ ዓይን የታየኝ ጉድለት የለም። በውስጡ ያየኋቸው ነገሮች ታማኝነት ፤ እውነተኛ ኢትዮጵያዊነት ፤ የደራሲው ግልጽ ባሕርይና በስሜት ከመነዳት መራቅ ፤ እጅግ ጠቃሚ ትምህርት፤ ትክክለኛ ዳኝነትና የመሰሉት ስለሆኑ ፤ ሌላውን ነገር ለማሰላሰል ስሜቴ ጊዜ አልሰጠኝም።
ስለመጽሐፉ ጐደለ ብዬ የምናገረው ነገር ቢኖር አንድ ብቻ ነው። ይኸውም ይህ ታላቅ ትምህርት እንደታላቅነቱ በቆዳ ሽፋንና በወርቅ ቀለም በጥሩ ወረቀት መቅረብ የተገባውን ያህል በትንሹ ታላቁ ፤ በደሀው ፤ በሀብታሙ ኢትዮጵያዊ መነበብ ደግሞ ስለሚገባው ፤ ተራ ወረቀትና ጥራዝ ፤ ታትሞ አለመቅረቡ ነው። ስለዚህም ደራሲው ወይም መብቱን የተረከበው ድርጅት እንደሚያስብበት ተስፋ አደርጋለሁ።
የኔ ስሜት ይህ ነው። በዚህም የግል አስተያየቴን ገለጽሁ እንጂ በሌላው የግል ፍርድ አልገባሁም።
