የህሊና ደወል ሂስ ሰይፉ መታፈሪያ


✍️✍️✍️✍️✍️


ደራሲ - በዓሉ ግርማ

የመጽሐፉ ርዕስ - የህሊና ደወል

ሃያሲ  - ሰይፉ መታፈሪያ

ጽሑፉ የወጣበት ቦታ - መነን መጽሔት

ዘመን - ሰኔ 1966 ..


✍️✍️✍️✍️✍️


ታሪኩ 


ባለ ስድስት ክፍል ትምህርት ቤት፣ ቤተ ክርስቲያን፣ የፖሊስ ጣቢያ ብጤና የባላባት መኖሪያ ፎቅ ቤት ከጥቂቶቹ የሣርና የቆርቆሮ ቤቶች ጋር ተዳምረው ሱጴ ቦሮን ይሆናሉ — ከኢሉባቦር ትንንሽ ከተሞች አንድዋ። ከነዋሪዎቹ ካራት መቶ እማያንሱት ተማሪዎች ናቸው። ከትምህርት ቤቱ ውስጥ ያሉት ቦታ ጠብዋቸው፣ ከውጭ ያሉት ሕፃናት ደግሞ ለመግባት እያሰፈሰፉ የትምህርት ቤት ጉዳይ ፥ የሱጴ ቦሮ የመጀመሪያው ኅብረተሰብአዊ የውስጥ እግር እሾክ ሆንዋል። 


በአካባቢው ቡና አብቃይነት፣ በሞያተኛነትም ቢሆን፣ ሕዝቡ ሳንቲሞች በኪሱ ያንቃጭላል። የሳንቲም ቀጨልጨልታው ደግሞ፣ በተራው፣ የብርሌ ደቅደቅታ፣ ደቅደቅታው ሣቅና ጨዋታ፣ ሣቅ ጨዋታው ደግሞ ውስጥ ውስጡን ሠርጎ የሚመጣ የስለት መፋጨት ይጠራል። ባናት፣ የቃልቻው የአባ ጨፌ ድቤ ድልቅታ ውቃቢያዊ ገላጋይና ከለላ መስሎ ፥ ባጋጣሚው እየተጠቀመ ይህን በድምፁ የተምታታ የሱጴ ቦሮ ከተማ ይበልጡን ያምታታል።


በእንዲህ ያለው የተምታታ ሁኔታ ውስጥ አድባርዋም ብትሆን የሚላስ የደም ጠብታ አታጣም። ዱሮማ ለድርቅና ለቸነፈር እየተባለ ከሚፈሰው የነጭ ኮርማ ደም ሌላ፣ የኖጳና የሱጳ ዝርዮች ጠብ ብዙ ይገብርላት ነበር። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን፣ ከነዚህ ሁለት ቤተሰቦች፣ አንዱ ላንዱ ታጥቆት ውሎ ተንተርሶት ያድረው የነበረው የቂም በቀል ሱሬ ደም፣ ቅላቱ ወደመንጣት እየሄደ ተናዳለች። ለዚህ ምክንያቱ የሱጳን ዝርያ፣ የፊታውራሪ ተካን ልጅ ዓይናለምን ለልጃቸው ለዳኛቸው የለመኑት የኖጳው ዝርያ ፊታውራሪ አያና ናቸው። አሠሥ ገሠሡ ብዙ ነው — ይህ ሙዋርታዊ የኑሮ መልክ የሱጴ ቦሮ ሁለተኛው ኅብረተሰብአ ዊ የውስጥ እግር እሾክ ነው። 


ሱጴ በዚህ ሁኔታ እንዳለች መሲሕ ይመጣላታል — ሐዲስ ሳህሌ ። ሐዲስ የሙዋቹ የመምሬ ሳህሌ ልጅ ፡ ከሕፃንነቱ ጀምሮ በእናት እጅ፣ በመጨረሻው የድኅነት ደረጃ ያደገ፣ ከሁለተኛ ደረጃ በማዕረግ ተመርቆ አሁን የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የሁለተኛ ዓመት ተማሪ የሆነ ነው። አሁን ሃያ ሰባት ዓመት ሆኖታል ፤ በግል ምክንያት በእልቄ ቅድስት ማርያም ትምህርት ቤት፣ ላንድ ዓመት አስተማሪነት ተቀጥሮ መጥቶአል። 


መጥቶ አራት ወር ሳይሞላው፣ ሰባት ዓመት ሙሉ የትምህርት ቤትዋ ድሬክተር ከሆኑት ከአቶ ይርጋ ዓለሙ ጋር፣ የሐሳብ ሽኩቻ ጀመረ። የሽኩቻው ጥሬ ምክንያት የማስተማሪያ ክፍል አንስዋልና አሁኑኑ! እናሠራ ነው— ሐዲስ እንደሚለው፣ ቆይ! ታገሥ! ቀስ በል! ነው — አቶ ይርጋ እንደሚሉት። በሙዝ የተጠቀለለ ኮሶ ይመስል ፥ በጥሬ ምክንያቱ ውስጥ የተደበቀው መራሩ ምክንያት — በዘመናዊ አነጋገር — የአድኀሪና የተራማጅ ጠብ ነው። “እስመ ግብሩ ይመርሆ ኀበ ስሙ” እንዳሉ — ይርጋ አድኅሪ ሐዲስ ደግሞ ተራማጅ ናቸው። ጠቡ በትንሽ መንደር ደረጃ ይወሰድ እንጂ ብሔራዊ ነው። 


ይርጋ “አዲሱን መሲህ” ለመጥላት ሁለት ተደጋጋፊ ምክንያቶች አሉዋቸው ፦ አንድ በሚስቴ መጣህ የሚያሰኝ ዓይነት ነው። ስለሱም ባንድ አጋጣሚ እንዲህ ይላሉ :- ትምህርት ቤትዋን “...እንደ ዓይኔ ብሌን ነው የማያት። ሌላ ፍቅር አላውቅም። ፊትዋን ያዞረችብኝ መሰለኝ። ..ገዴ ነበር የምላት።” የይርጋን ስሜት የሚያውቅ መቶ አለቃ አሽኔ “... ትምሀርት ቤትዋን እንደሚስትህ ትቀናባታለህ ..." ብሎአቸዋል። ሁለተኛ ፡ ሚስት ከተነካች ክብር ተነካ ነውና ፡ ይርጋ ክብሬ ተነካ ይላሉ። ይህንንም ሲያብራሩ ፣ “...እኔን እንደ ሻገተ እንደ ዛገ ዕቃ ቆጥሮኝ ሥራውን ጀመረ። ከጀመረም በኋላ አንድ ቀን አላማከ ረኝም። ይቅርታ አልጠየቀኝም። እኔ ሥራውን ሳይሆን ንቀቱን ነው የምቃወመው . . .” ይላሉ። 


ይርጋ ሐዲስን ለማጥፋት ብዙ አድርገዋል ፡- የቢሮ ነገር ጉንጎና፣ ሙዋርት፣ ኩሊዎችንና ወዳጆችን በላዬ ማስነሣት፣ በዲቃላ አስረጋዥነት ለማስከሰስ መሞከርና የብርሌ ጉዋደኞቻቸውን ጣቶች በሱ ላይ ማስቀሰር። 


ሐዲስ ግን በመሲሕ ሞዴል የቀረበ ነውና ይህን ሁሉ ታግሦ የአዋጅ ነጋሪ መላክተኛነቱን ሕይወት ይቀጥላል — የሦስትያ ተወጥሮ። እሱ ከማሕል ነው። ወጣሪዎቹ እናቱ፣ አይናለምና ትምህርት ቤቱ ናቸው። ሥጋውን የገዛችው አንዲት አራተኛ ሴትም አለች-መጠጥ አሻሻጭዋ ሽታዬ። ሽታዬ በፍላጎትዋ በጣም ግለኛ ናትና እንደ እሳት እራት ስትዞረው፣ ከሦስቱ ማሕል የሚወጣው የስሜት ነበልባል ያሳርራታል እና እንዲህ የውጥሩን ኢትዮጵያን እያሰበ ቀናትን ይቀያይራል — ኢትዮጵያንም በተራዋ የሦስትያ አስወጥሮ። ወጣሪዎቹ የተማረው ወገን ግብዝ የአእምሮ ሰውነት፣ ሥልጣን የጨበጠው ወገንና በጎሣ ልዩነት የ ተጠመደው ሕዝብ ነው። “አዲሱ መሲህ” በኢትዮጵያ ስም ኢትዮጵያውያን ግለሰብ ያስባል — ይህንንም ግለሰብ የሦስትያ አስወጥሮ። ወጣሪዎቹ አእምሮ፣ ሕሊናና እጅ ናቸው። ይህ የሐሳብ አቀራረብ ክርስቶስ ከሦስቱ አንዱ እንደመሆኑ ሥላሴን ያሳስባል። 


አዲሱ ክርስቶስ ዮሐንስ መጥምቁንም ሆኖ የአዲሱን ሃይማኖት የስርየት አዋጅ ነገራ ይጀምራል። ታርዛንና የቀሩት ኢትዮጵያውያን ሁሉ እጃቸውን አስንፈው “አፈወርቅ ተክሌ የሚስላቸውን ጣቶች” አስመስለዋቸዋልና በድለዋል። በደሉ የመጣ በእጅ ስንፍና ከሆነ የበደሉ ስርየት እጅን በሥራ ላይ በማዋል ነው። በሌላ አነጋገር አዲሱ ክርስቶስ ዮሐንስ መጥምቁንም ሆኖ የአዲሱን ሃይማኖት የስርየት አዋጅ “ያፍ ብልኀት ጌትነት ፡ የእጅ ብልኀት ባርነት” የሚለውን የኖረ ፍልስፍናችንን እንለውጥ ነው። ክርስቶስ ኒቆዲሞስን እንዳለው ዓይነት፣ የዚህ ሃይማኖት አባል ለመሆን "... በሥራ እንደገና መወለድ ያስፈልጋል።" 


አዲሱ መሲህ አከታትሎ ስለ ፍቅር ይሰብካል “ፍቅር ... ሁሉን በእኩልነት ደረጃ የሚመለከት ከፍተኛ ሃይማኖት ነው። “ፍቅር እግዚአብሔር ነው።” ፍቅር ካለን “እያንዳንዳችን እግዚአብሔር እንሆናለን በየቤታችን። ” የዚህ ፍቅር መሰላሉ እውቀት . . . የእውቀት መሰረቱ ደግሞ ትምህርት ቤት ነው።” በቅዱስ ጳውሎስ አነጋገር ዓይነት፣ ይህ ፍቅር ከሌለ ሃይማኖት የለም ፤ ሌላው ያለውም ሁሉ ከንቱ ነው። እንዲሁም በክርስቶስ አነጋገር ዓይነት ሞቼ በሦስተኛው ቀን እነሣለሁ የሚል ይመስል—ባንድ ሁለት አጋጣሚዎች “አልሻግትምገና አብባለሁ” ይላል። በገዳመ ቆርንቶስ የተገኘ ይመስልም፣ በፍቅረ ነዋይ ይፈተናል። በመጨረሻው፣ ይርጋ ዓለሙን ገድለሃል ተብሎ ይያዛል። ሲያዝም ፖሊሶች እጆቹን ሲያስሩት አሰሩኝ እንዳይል “እጆቼ ከተቸነከሩ ኤሎሄ ኤሎሄ ከ ማለት ሌላ ምን ቀረኝ ይላል — ክርስቶስን መምሰሉን ሲያሙዋላ። 


ስቅለቱ ዓርብ በስድስት ሰዓት ይሆናል። “አዲሱ መሲህ” ከእሥር ቤት ወደ ስቅለቱ ሲወሰድ ፈያታዊ ዘየማንን ይመስል- ከአብሮ ታሳሪዎቹ አንዱ “ሳይህ በደል የሚሠራ ሰው አትመስለኝም። ግን ክርስቶስም ያለበደሉ ተሰቅልዋል .. ” ይሉታል። ከመስቀያው ቦታ ሲደርስ በክርስቶስ የደረሰው “ስቀለው! ስቀለው !” ጩኸትና የጲላጦስ እጁን መታጠብ ታውሶታል። 


የመስቀል ላይ ይቅርታውን ቀደም ብለው ፊታውራሪ ተካ ተናግረውለታል ፡- "የረ ገሙህንና የተፉብህን ሁሉ ይቅር በላቸው፣ ባያውቁ ነው ...”። በመስቀል ላይ ጥቁር ዐፈር ይቀምሳል - ቁርባን ይመስል። በርሜሉ ከሥሩ ተገፍቶ ሲንጠለጠል ከእንቅልፉ ይነቃል — የቅዠት ነገር፣ ስንቱን አየው ! የሆነው ሆነ በሕልሙም ሆነ በውኑ “አዲሱ መሲህ መሲሕነቱን አሙዋላ፣ አሣመረም። 


በዕውነተኛ የይርጋ ዓለሙ ገዳይነቱ፣ ቶሎሳ እጁን ሰጥቶ፣ ሐዲስ ይፈታል። ሐዲስ እንደተፈታ ትምህርትቤቱ ያልቃል — አዲሱ “... ቤተ እግዚአብሔር ...“። መለኮታዊ ኃይል፣ ይህ አዲስ ቤተ እግዚአብሔር ላለቀበት ለዚህ ቅዱስ ቀን ምሥራቻዊ መስዋዕት እንድትሆን ያቆያት ይመስል፣ በመጀመሪያው የጫጉላ ሙከራ የከሸፈበት ፈቃደ ሥጋውም ተነሣሥቶለት ክብርናዋን ይገሣል — ነገሩ ሰብአዊ አልመስል አለ። ከመጀመሪያው እስካሁን በተባለው አንድ አንድ ሊመለከቱ የሚገቡ ነጥቦች አሉ። 


አስተያየት 


አንደኛ በታሪኩ ውስጥ አንዳንድ ሁኔታዎች አሉ። እነሱም በነገር ተደጋግፎ የተፈጥሮ ክንብንባቸውን አውልቀውና ወዲያ ጥለው ለኛ በመታየት ፈንታ ድርሰታዊው ባለጅ ላንድ ዓላማ አበጃጅቶ አስገድዶ ያቀረበልን ይመስላሉ። ከነዚህም ለምሳሌ ፥ በቀጠሮ መፍረስ ምክንያት የሙሽራውን ከበር መመለስ ፥ የሐዲስን የጫጉላ ቤት ክሽፈትና የቶሎሳን ሁልገብ ጉብዝና እጠቅሳለሁ። 


ሁለተኛ የሐዲስ አለቅጥ ክርስቶስን መ ምሰል፣ በብሔራዊ ዕድገት ሥራው፣ አንድ ግራ እሆነ ሁኔታ ውስጥ የጨመረው ይመስለኛል ፡- የሐዲስን የመስዋዕትነት ዓይነትና የክርስቶስን የመስዋዕትነት ዓይነት በመስዋዕትነታቸው ሊያስገኙት የሚፈልጉት የዓለም ዓይነት ይለያቸዋል። የክርስቶስ ዓለም ሰማያዊ ነው — የጦር መሣሪያ አያስፈልገውም። የሐዲስ ዓለም ግን ምድ ራዊ ነው — አህያ ይመስል አለ ዱላ ወደፊት የማይራመድ። ለዚህ ባለፉት አምስት ወራት በሦስት ሺህ ዓመታት የተረጋጋ ዕድሜዋ በምትኮራው ኢትዮጵያ ውስጥ ለሆነው እንቅስቃሴ ምክንያት የሆነው ነገር ማስረጂያ ነው። 


በዚህ የነገር አቀማመጥ ላይ የተመሠረተው ግራ ነገር እንዲህ ነው። ሐዲስ በክርስቶስ ሞዴል የተፈጠረ ባሕርይ እንደመሆኑ፣ ይቅር ባይ ነውና ስለዋና ጠላቱ ስለ ይርጋ ዓለሙ ሲጠያየቁ “እኔ ያለቃ ጠላት የለኝም።” ይላል — ለመቶ አለቃ አሽኔ። እንደ ዕውነቱ ግን በአድኀሪዎችና በተራማጆች ለተከፈለው “የህሊና ደወል” ዓለም ለወገን መሪነታቸው እንደ ጎልያድና ዳዊት ሊጋጠሙ የሚገባቸው ሁለቱ ናቸው። በዚህ ነገር አያያዙ ፥ ሐዲስ፣ አለቅጥ ሰላማዊ (ፓሲፊስት) ሆንዋልና ዘመናዊውን ተታጋይ ተማሪ አይወክልም። ይልቅስ በናቱ የሙት ቃል ወይም በሌላ የውጭ ኃይል ተጠምዶ፣ እንደ ነቢዩ ዮናስ በተጠመደበት ሥራ የተገደደ ይመስላል። 


ሦስተኛ፣ ሐዲስ፣ ብዙ ይፈላሰፋል። ለምሳሌ በፊታውራሪ ተካ የሠርግ ዳስ ውስጥ በመቱ ቡና ቤትና በሌሎች አጋጣሚዎች እሱን ማየት ነው። 


ከሚያመጣቸው ሐሳቦች አንዳንዶቹ በአንባቢ ላይ የክርክር ፈለማ ይቀሰቅሳሉ። ከነዚህ አንዱ ስለ ፍቅር የተባለው ነው። እዚህ ስለ ፍቅር በተሰጠው ትንተና፣ በመመሳሰል ወይም በአንድ ዓይነትነት የተሰጡ ሁለት የፍቅር ዓይነቶች አሉ። የመጀመሪያው የቅዱስ ጳውሎስ ነው :- “ተራሮችንም እስካፈልስ ድረስ እምነት ሁሉ ቢኖረኝ ፤ ፍቅር ከሌለኝ ከንቱ ነኝ።” ይህ የ ትሩፋት ነገር ነው። ሁለተኛው “የፍቅር መሰላሉ እውቀት — የእውቀት መሠረቱ ደግሞ ትምህርት ቤት ነው። ትምህርት አዲሱ ቤተ እግዚአብሔር ነው ...” እሚሉት ቃላት ውስጥ የተያዘው የፍቅር ዐይነት ነው። ይህ ሁለተኛው ዓይነት ፍቅር ትምህርት ቤት የምታሳውቀን የሌላውም የኛም መብት ነው እንጂ ፍቅር አይደለም። አንዳንድ ጊዜ እንደሚሰማው፣ ትምህርት ዓይናቸውን የከፈተላቸው የቅኝ ተገዢዎች ክርስቲያኖች ቅኝ ገዢዎቻቸውን፣ ጳውሎሳዊ ፍቅራችሁን ለራሳችሁ አድርጋችሁ ትምህርታዊ መብታችንን ስጡን ይላሉ። ሐዲስ በመሲሐዊ ስሜት እየተወሰደ እነዚህን ሁለት የፍቅር ዓይነቶች አይለይም። 


አራተኛ “የህሊና ደወል”ን በአጠቃላይ ሳስበው ለሞንድ የፈረንሳይኛ ጋዜጣ ከጥቂት ዓመታት በፊት ስለ እስፓኝ ደራሲዎች የሰጠው አንድ አስተያየት ይታወኛል። ሐሳቡ እንዲህ ነው ፤ የሐሳብ ነፃነት በሌለበት አገር፣ ጋዜጠኞች ነገርን አፈራርጠው ስለማይጽፉ ደራሲዎች በልብ ወለድ ድርሰት ከለላ ከኅብረተሰብ ችግሮች ጋር ትንንቅ ይጀምራሉ። በዓሉ እንዲህ ያለ ነገር የደረሰበት ይመስለኛል። 


የመጽሐፉ እምብርት ሐሳብ ብሔራዊ ለውጥ በትምህርት የሚል ነው። ከለውጡም ሐሳብ ጋር ተያይዘው መሠረታዊ ለውጥ፣ ለውጥ ያለ ደም መፋሰስ፣ ትምህርት የብሔራዊ ዕድገት በር፣ ያልተዳቀለ ንጥር ብሔራዊ ያለዋወጥ ዓይነት፣ ፍትሕ፣ ኅብረተሰብአዊ ፍቅር፣ የተማረው ሕዝብ ስንፍና፣ የጎሳ ልዩነት ችግር የሚሉና ሌሎችም የሐሳብ ዝርዝሮች ይመጣሉ። በተለየ ባለፉት አራት አምስት ወራት ውስጥ፣ እነዚህና ሌሎች እነዚህን የመሰሉ በየጋዜጣው እንደ ክረምት ፀሐይ ብልጭ ድርግም ሲሉ ከርመዋል። ከዚያ በፊትማ፣ በተለየ የጎሳ ጉዳይ እንዲሁ በየልብወለድ ድርሰቱ ካልሆነ ጨርሶ አይነሣም ነበር። 


እንደሚመስለኝ ፣በዓሉ፣ በዚህ የፈጠራ ድርሰቱ ሊገልጻቸው የፈለጋቸው የሐሳብ ዓይነቶች ቀደም ብለው ኖረውት፣ እነዚያን ለመግለጽ፣ ታሪክ ፈጥሮአል። ይህ ኪነታዊ ዋጋን ይቀንሣል። በዚህ ረገድ “ከህሊና ደወል” ይልቅ “አድማስ ባሻገር” ይበልጥ ድርሰታዊ ኪን የሚያሳይ ሆኖ አግኝቸዋለሁ። 


ገለጻ፣ ቋንቋና ጽሕፈት 


“በህሊና ደወል” ውስጥ ለበዓሉ አዲስ ሆኖ ያገኘሁት፣ አንድ በሠዓሊዎች የምናየው የአገላለጽ ለውጥ ነው። ባንድ ዘመን፣ ሠዓሊዎች፣ ለምሳሌ የሰውን ፊት ሁለት በኩሉን (ግምባሩንና አንዱን ጆሮ ግንዱን) ያሳዩን ነበር። በኋላ ግን ያይን ግርፊያ ባንዴ ሊያይ የሚችለውን ሁሉ ለማሳየት ፈልገው፣ የሰውን ፊት ሦስት በኩሉን (ግምባሩንና ሁለት ጆሮግንዶቹን) ያሳዩን ጀመር — ላለመደው የስብርብር መሥመሮች ጥርቅም ነው። የዚያ ብጤ፣ በዓሉም ያንድን ቅጽበት የሕይወት መልክ ፣ ምኑም ምኑም ሳይቀር ሊያሳየን ይሞክራል። ለምሳሌ በወይዘሮ ዝናሽ መጠጥ ቤትና በስቅለቱ ቦታ የታየው ቅጽበታዊ ሕይወትን በተጠቃሎዋ ያሳያል ። ይህም ሲሆን እንደ ስብርብሩ የመሥመር ጥርቅም የዓረፍተ ነገሮቹ ዓይነትና የሥርዓተ ነጥቡ ነገር እንግዳ ሆኖ እናገኘዋለን። ስለዚህ ዓይነቱ አገላለጽ፣ የዓረፍተ ነገሩንና የሥርዓተ ነጥቡን ጉዳይ ጨምሮ፣ ካንድ የሚጨበጥ አስተያየት ለመድረስ፣ በዳኛቸው ወርቁ “አደፍርስ” ውስጥ ከሚያሳየው መልኩ ጋር አጣምሮ መመልከት ያስፈልጋል። ከዚሁ ጋር አያይዞ — እኔ እዚህ ያላደረግሁትን ነገር — ስለ በዓሉ የዓረፍተ ነገር አሠራር አስተያየት መስጠት ይቻላል። 


በተቀረ አድማስ ባሻገር ውስጥ ያወቅነው በዓሉ እዚህም አለ :- የሰው ለሰው ግንኙነትን ማንም ኢትዮጵያዊ ደራሲ እንደሚያደርገው በጥሬው ያሳያል ፣ በተረትና ምሳሌ በጣም ይጠቀማል ፤ ከምሳሌያዊ መግለጪያዎቹም ለምሳሌ የምቡዋይ ካብ እንደግመል ሽንት ደመ መራራና ሌሎችም ባህላዊ የሆኑ አሉ። በትረካው ውስጥ፣ ካን ዱ ወሬ ወደ ሌላው ሲሸጋገር፣ የሚያመጣቸው የወሬ መቁዋጠሪያዎች ወይም ድልድዮች ድንገተኞች ናቸው። ድንገተኞች በመሆናቸውም አንባቢን ይቀሰቅሳሉ። ለዚህ የቶሎሳን የፍቅር ማጨናገፍ የሙሽሪት ነጣቂው ሙሽራ ተኩስ የተነጠቀችውን ሙሽሪት አስመላሽ ቡድን አደጋ አጣጣልና የአቶ ይርጋ ገደላ አጠነሳሰስን እንደምሳሌ መውሰድ ይቻላል። 


በጠቅላላው “የህሊና ደወል” ቋንቋ የጽሑፍ ሳይሆን የንግግሩ ነው። ለምሳሌ “ተወረወረ እኮ” ብሎ ከመጻፍ ፈንታ “ተወረወረ'ኮ” ይላል። የ"እ” አወዳደቅ የሚያጠያይቅ ቢሆንም፣ ወደ ሕይወት ጥሬ መልክ ያቀርበናልና፣ ምርጫው የሚደገፍ ነው። ይህ ሆኖ ሳለ ግን፣ ለምሳሌ አልፎ አልፎ፣ “ደባትር” ጠብ መንጃ፣ የንቅስቃሴ ኡደት፣ ያሳብ ኡደት፣ የቡና ኡደት፣ ቅጽረ ግቢ፣ ህልውና በለሆሳሳና በእዝነ ህሊና አየ ሲል ይገኛል። በነገራችን ላይ ሰው በእዝነ ሕሊናው ይሰማ እንደሆን እንጂ አያይም። ክርስቶስ ሳምራ የተባለውም ክርስቶስ ሰምራ ነው። 


ቀጥሎ ወረቀት ላይ ጥቁረታቸውን ደጋግመን ያላየነው ሀራም (እርም)፣ ተዘናፍሎ (ዘንፈል ብሎ ወድቆ)፣ ቱማታ (ሆይ ሆይታ)፣ ነጃሳ (በሽታ)፣ አማተረ (ከላይ እታች ተመለከተ)፣ አወናጨፈ (አመሳቀለ)፣ ክብሳት (ቁልል)፣ ሰምበታ ጐዳና (እሑድ)፣ ዲቤ የሚሉትን ቃላት እናገኛለን። ጥሁት፣ ይንቃጨጫል ወይም ሲባል እንደሰማሁት፣ ይንቀጫቀጫልና የእንቁራሪቶች ቁርርታ የሚሉት ትርጉማቸውን የሚጮሁ ቃላት ናቸው።  


እንደ ሌሎች ልብ ወለድ መጻሕፍት፣ “የህሊና ደወል”ም ድርብ ፊደሎችን እየቀነሰ የተጻፈ ነው። ነገር ግን ለምሳሌ በፍቅር እስከ መቃብር ከ“ጸ” ና ከ“ፀ” ሁለተኛው ሲጣል “በህሊና ደወል” የመጀመሪያው ተጥልዋል። በሌላ በኩል “ፍቅር እስከ መቃብር” በሚያስፈልጉበት ሁሉ ቃላትን በዲቃሎች ፊደሎች ሲጽፍ የህሊና ደወል ባንዱ መንገድ አልረጋም። ማለት “እንኳንም” ፣ “በሁዋላም” ብሎ ይጽፋል። ይህ በደራሲዎች ማህል የሚታይ የሐሳብ ልዩነትና ባንድ መንገድ አለመጽናትን ያሳያል። እንዲሁም ስለ ጽሕፈት መንገዳችን ስምምነት እንዲኖር፣ አንድ ነገር ማ ድረግ እንዳለብንም ይገልጽልናል።


መደምደሚያውን 


በዓሉ ባራት ዓመታት ውስጥ ሁለት መጻሕፍት መጻፉ ነው። ከነዚህም አንዱ በሁለት ዓመቱ ሁለቴ የመታተም ዕድል አጋጥሞታል። ይህ ለደራሲነቱ ደኅና ምልክት ነው። የሁለተኛውን መጽሐፉን ታሪክ ደግሞ በኦሮሞ ባህል ስለቀለመው፣ ለድርሰት ዓለማችን ውስጥ፣ ደራሲዎች እስከዚህም ያልተመለከቱትን አቅጣጫ ወስድዋል። ይህ ጥሩ ነው ፡- የሐሳብ አድማሳችንን ያሰፋል ፤ ቋንቋችንንም ያዳብራል። ሆኖም ግን የፈጠራ ሥራ፣ ተኩስ ይመስል፣ ሁሌ አይሳካም። ዋናው ነገር የደራሲነት ትርታው ሳያቋርጥ መምታቱ ነው። ትርታ የሕያውነት ምልክት ነው። ደራሲው ሕያው ከሆነ ደሞ አንድ ቀን ልባዊ የሐሳብ ቦግታ ሊያጋጥመው ይችላል። እና ያድማስ ባሻገርን ደረጃ የሚጠብቅ ሦስተኛ መጽሐፍ ተስፋ እያደረግሁ ጽሑፌን አቆማለሁ።

ስለ ጸሐፊው/ዋ እርሶ የሚያውቁት የተለየ ነገር ካለ፣ እዚህ ሲጠቀስ የጎደለ ነገር ከተሰማዎት፣ አዲስ ተጨማሪ ስራ ሲያገኙም ኮመንት መስጫው እርሶን እየጠበቀ ነው።

Comment

Ads

advert
advert